የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ህወሃትን ከተፎካካሪ ፓርቲነት ሲሰርዝ ለ6ተኛው አገራዊ ምርጫ ጸጥታን ማረጋገጥ እንዲሁም የምርጫ ክልል እና የዞን ቢሮዎችን ለመክፈት ለክልሎች ላቀረበው ጥያቄ በቂ ምላሽ ማግኘት አለመቻሉን ገለጸ፡፡
ቦርዱ በህግ የተሰጠውን ፓርቲዎችን የመከታተልና የመቆጣጠር ስልጣን ተጠቅሞ ህዝባዊ ወያነ ሐርነት ትግራይ (ሕወሃት) ኃይልን መሠረት ያደረገ የአመጽ ተግባር ላይ መሣተፉን በማረጋገጡ እና ፓርቲውን እና ቦርዱን በማገናኘት ይሰሩ የነበሩትን የአዲስ አበባ ተወካይ ለማነጋገር ጥረት ቢያደርግም ግለሰቡ ፍቃደኛ ባለመሆናቸው የፓርቲው ኃላፊዎች በፓርቲው ስም መንቀሳቀስ እንደማይችሉ ውሳኔ ማሳለፉን ተናግሯል፡፡
ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከዚህ ባሻገር በክልሉ የሚንቀሳቀሱት ዓሲምባ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ ብሔራዊ ባይቶ አባይ ትግራይ /ባይቶና/ እና ሳልሳይ ወያነ ትግራይ /ሣወት/ በትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ውስጥ በተካሄደ ህገወጥ ምርጫ ስለመሳተፋቸው ማብራሪያ እንዲሰጡ መጠየቁንም አስታውቋል፡፡ ቦርዱ አዲሱን ሲዳማ ክልልን ጨምሮ ለሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የምርጫ ቢሮዎች፣ የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎችና የስልጠና ቦታዎችን እንዲያሳውቁት ጠይቆ ምላሽ እንዳልሰጡት ተናግሯል፡፡
እስከ ሰኞ ቀን 10/05/2013 ድረስ የምርጫ ክልሎች ዝርዝር ቢሯቸው የሚቋቋምባቸው ከተሞች፤ የዞን ማስተባበሪዎች እና ቢሮአቸው የሚቋቋምባቸው ከተሞች ዝርዝር እንዲሁም ቦርዱ ያወጣውን ረቂቅ የምርጫ ሰሌዳ ኮፒ አድርጎ መላኩን ጠቁሟል። ይሁንና በተጠቀሰው ጊዜ ምላሽ የሠጠ ፓርቲ እንደሌለ ምርጫ ቦርድ ገልጧል፡፡
*********************************************************************
ቀን 12/05/2013
አሐዱ ራዲዮ 94.3
ምስል፡- የአሐዱ ሎጎ
The post ምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልል እና የዞን ቢሮዎችን ለመክፈት ለክልሎች ላቀረበው ጥያቄ በቂ ምላሽ ማግኘት አልቻልኩም አለ፡፡ appeared first on አሐዱ ቲቪ እና ራድዮ 94.3.
Source: Link to the Post