
ሰበር ዜና! የማክሰኝት ከተማን የተቆጣጠረው የአማራ ፋኖ በጎንደር ዙሪያ በአገዛዙ አፈና ስር የቆዬውን ፋኖ አደባባይ አበበን መረከቡን አስታወቀ። አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ … ሀምሌ 11/2015 ዓ/ም_አዲስ አበባ ኢትዮጵያ በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ጎንደር ዙሪያ ወረዳ የማክሰኝት ከተማን እና አካባቢውን ሀምሌ 11/2015 ከጠዋቱ 1:10 ሰዓት ጀምሮ ከወጣቶችና ከህዝቡ ጋር በመቀናጀት በቁጥጥር ያዋለው የአማራ ፋኖ በጎንደር ዙሪያ ሀምሌ 10/2015 በግፍ አርባያ መገንጠያ ላይ በአገዛዙ ጦር ታፍኖ ወደ ጎንደር የተወሰደውን የፋይናንስ ክፍል ተጠሪውን ፋኖ አደባባይ አበበን አስለቅቋል። በብልጽግና ካድሪዎች ሽምግልና የተጠየቀው ፋኖ አለሙ ጎዳዳው የሚመራው የአማራ ፋኖ በጎንደር ዙሪያ በግፍ ያፈናችሁትን ፋኖ አደባባይ አበበን በቅድሚያ ስትለቁ እንነጋገራለን ማለቱ ይታወሳል። ይህን ተከትሎም የተለመደውን ጸረ አማራ የኃይል መንገድን የመረጡ የማዕከላዊ ጎንደር ዞን የብልጽግና ካድሪዎች ከተለያዩ አቅጣጫዎች የአገዛዙን ጦር በማስጠጋት ወደ ጦርነት እየዘመቱ ባሉበት ጸዳ ላይ አንድ ፓትሮል ሙሉ ጦር ከእነ ትጥቁ መማረኩን ተከትሎ አደባባይ አበበን ለመልቀቅ መገደዳቸውን ነው የአሚማ ምንጮች የገለጹት። በዚህም መሰረት የአማራ ፋኖ በጎንደር ዙሪያ አመራሮች እና አባላት ጉማራ ወንዝ አካባቢ ፋኖ አደባባይ አበበን ተረክበው ወደተቆጣጠሯት ከተማ ማክሰኝት ይዘው መግባታቸው ታውቋል። አሁን ላይ የማክሰኝትና አካባቢው ወጣቶች ከአማራ ፋኖ በጎንደር ዙሪያ አመራሮችና አባላት ጋር እየመከሩ መሆናቸው ታውቋል። አሚማ ከፋኖ የቅድመ ሁኔታ ጥያቄ መመለስ በኋላ ምን ምን ጉዳዮች በህዝባዊ ኃይሉ ፋኖ፣ በወጣቶች እና በህዝቡ እንደተነሱ ታማኝ ምንጮችን ለማነጋገር ሞክሯል። የአማራ ፋኖ በጎንደር ዙሪያ ከማክሰኝትና አካባቢው ወጣቶች እንዲሁም ነዋሪዎች ጋር አደባባይ ላይ በስፋት ከመከረ በኋላ በበርካታ አበይት ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት መፍጠሩን አስታውቋል። ሽምግልና እየላኩ ለሚገኙ የብልጽግና አገዛዝ ካድሪዎች እንዲነገራቸው በሚል የሚከተሉትን የጋራ ነጥቦች አስቀምጠዋል:_ ይኸውም:_ 1) በፋኖ እና በህዝብ ይሁንታ ወደ ማክሰኝት ከተማ የሚገቡ የአካባቢው መስተዳድር አካላት ፋኖ ነህ፣ የፋኖ ደጋፊ ነህ፣ መንገድ በመዝጋት ተባብረሃል እንዲሁም ሌላም ሰበባ ሰበቦችን እያነሱ እንዳያፍኑ፣ እያዳያስሩ፣ እንዳያሳድዱና እንዳያስፈራሩ በሚለው ጉዳይ እንዲስማሙ ይደረግ ተብሏል። ይህ የጋራ ስምምነት ከተጣሰ ግን ፋኖ ራሱንና ወገኑን ለመከላከል ሲል ለሚወሰዳቸው ማናቸውም እርምጃዎች ኃላፊነቱን የካድሪዎች ይሆናል። 2) የአማራ ህዝብ ወይም ፋኖ በየትኛውም የወረዳው አካባቢዎች እንዳይንቀሳቀስ፣ እንዳይደራጅ እና እንዳይሰለጥን የሚያደርግ የስርዓቱ አካል እና አሰራር ሊኖር አይገባም። አማራ ህልውናን ለማስከበር ለሚያደርገው ስልጠና እና እንቅስቃሴ የማንንም ካድሪ ፍቃድ እና ይሁንታ ሊጠይቅ አይገባውም። ይህ ከተጣሰ ግን አሁንም ተጠያቂነቱ የህዝባዊ ኃይሉ ሳይሆን የአገዛዙ ስልጣን ጠባቂዎች ይሆናል። 3) ለዘመናት እየተጠየቁ ያሉ እና ከፍተኛ የሆነ የጅምላ ፍጅት የተፈጸመባቸው፣ መሳደድ እና መፈናቀል ሲፈጸምባቸው የኖሩ የአማራ የማንነት እና የአጽመ እርስት ጥያቄዎች እንዳይመለሱ በሚል የህወሓታዊያን እና የኦነጋዊያን ድብቅ ሴራ ፈጽሞ ተባባሪ እንዳይሆኑ፣ 4) በአማራ ላይ በተለያዩ አካባቢዎች እንደአብነትም ከሰሞኑ በተቀናጀ መልኩ ከባድ መሳሪያ በታጠቀ የአገዛዙ ጦር ይፋዊ ጦርነት የተከፈተባቸው የምስራቅ አማራ ፋኖ አመራሮች እና አባላት፣ በሰሜን ወሎ የራያ ቆቦ ነዋሪዎች፣ በደቡብ ወሎ የወግዲ ወረዳ ነዋሪዎች እንዲሁም እጅግ በተጋነነ የአስቸኳይ ጊዜ የሰዓት እላፊ አዋጅ የመንቀሳቀስ እና የመስራት መብቱ የተገደበበት የሸዋሮቢት ህዝብ እና በአማራ ፋኖ አንድነት በሸዋ ላይ እየተፈጸመ ያለው የለየለት ጸረ አማራ ግፍ እና በደል በአስቸኳይ እንዲቆም፤ በተመሳሳይ በምስራቅና በምዕራም ጎጃም የተለያዩ አካባቢዎች ህዝባዊ ኃይሉን ትጥቅ አስፈታለሁ በሚል በህዝቡ ጭምር እየተፈጸመ ያለው ስርዓታዊ አፈና፣ ግድያ፣ መፈናቀል እና መሳደድ እንዲቆም፣ እንዲሁም የአፈር ማዳበሪያ እና ምርጥ ዘር በመንፈግን ጨምሮ መላ አማራን በኢኮኖሚ የማድቀቅ አሻጥር፣ ከአማራ ክልል ውጭ የሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ በማንነታቸው ብቻ የኦህዴድ ብልጽግና አገዛዝ በስንቅ፣ በትጥቅና በመረጃ በአንድም ይሁን በሌላ መንገድ የሚደግፋቸው በአሸባሪ እና ወራሪ ኦነጋዊያን የሚፈጸመው የዘር ማጥፋት ወንጀል በስሙ እንዲጠራ ብሎም በአስቸኳይ እንዲቆም ፋኖ ከማክሰኝትና አካባቢው ወጣቶችና ነዋሪዎች ጋር ባደረገው ምክክር ላይ በስፋት ተነስቶ የጋራመግባባት ላይ ተደርሷል። ይህ አቋም የህዝባዊ ኃይሉ ፋኖ ብቻ ሳይሆን የህዝብ መሆኑ ታውቆ እንዲነገራቸው የሚል መግባባት ተደርሷል። እነዚህን የህዝብ ጥያቄዎች የማይቀበሉ ከሆነ የህዝብ የለውጥ ፍላጎትን ማዕከል አድርገው ለሚከሰቱ ማናቸውም ችግሮች ሁሉ ኃላፊነቱ የአገዛዙ ሰዎች እንደሚሆን በግልጽ ፋኖ እንዲነግራቸው ተስማምተዋል። የአገዛዙ ሰዎችም ፋኖ እና ህዝቡ ያነሳቸውን አንኳር ጉዳዮች ተቀብለው ለመፈጸም ዝግጁ ከሆኑ ወደነበሩበት አካባቢ እና ተቋማቸው መመለስ እንደሚችሉ ነው አማራ ሚዲያ ማዕከል (አሚማ) ከማክሰኝት ያነጋገራቸው ተሳታፊዎች ያረጋገጡለት።
Source: Link to the Post