///////
በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን ገጠሮች አካባቢ የተከሰተው ድርቅ አሁን ላይ ወደ ከተማም እየተስፋፋና እየተዳረሰ የሚገኝ ሲሆን እስካሁን የተከሰተው ድርቅ በቤት እንስሳት ላይ ያደረሰው ጉዳት እጅግ የከፋ ነው።
-በዞኑ ከነበሩ ከብቶች ውስጥ 90 ከመቶ የሚሆኑት ሞተዋል ብለው እንደሚገምቱ የአካባቢዎች ነዋሪዎች ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል፡፡
በዚህ የተነሳም አርብቶ አደሮች ባዶ እጃቸውን ቀርተዋል ነው የተባለው፡፡
-በድርቁ ምክንያት ከ800 ሺህ በላይ ሰዎች ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ መጋለጣቸው የዞኑ ነዋሪዎች ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል፡፡
-አሁን ላይ በድርቁ ምክንያት ከ378ሺህ በላይ የሚደርሱ ሰዎች ከቀያቸው ተፈናቅለው በ21 መጠለያ ጣቢያ ውስጥ እንደሚገኙም ተመላክቷል፡፡
ለእነዚህ ዜጎች እርዳታ ለማድረስ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝና ከአለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የጨመረ ቢሆንም ከተረጂ ቁጥር አንፃር እርዳታው አነስተኛ እንደሆነ ነዋሪዎች ለጣበያችን ተናግረዋል፡፡
ከምግብ እጥረት የተነሳ ህፃናትና አዛውንቶች ከፍተኛ ጉዳት ውስጥ እየገቡ መሆኑንም የገለጹ ሲሆን አሁን አሁን ሞት እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል፡፡
-አርብቶ አደሮች የተቀሩት ከብቶችን በህይወት ለማቆየት የቤታቸውን ጣራ ሳር እያነሱ ለከብቶቻቸው እየሰጡ መሆኑን የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል፡፡
በአሁኑ ሰዓት በገጠርም ሆነ በከተማ የምግብ እጥረት በከፍተኛ ሁኔታ አጋጥሟል ያሉት ነዋሪዎቹ የተራድኦ ድርጅቶች ከሚያቀርቡት ድጋፍ ውጪ እየቀረበ ያለ ድጋፍ የለም ብለዋል፡፡
-በዞኑ ኬር የተሰኝ የተራድኦ ድርጅት ለ600ሺህ ዜጎች ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ የገለጹ ሲሆን ከሌላ ወገን ድጋፍ የሚባል ነገር እየቀረበ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡
-በዞኑ ከነበሩ 3.3 ሚሊዮን ከብቶች ውስጥ አሁን በህይወት ያሉት ከ250ሺህ አይበልጡም ብለዋል፡፡
በዞኑ የተከሰተውን ድርቅ ተከትሎ ለዜጎች ድጋፍ እያሰባሰቡ የሚገኙ የአካባቢው ነዋሪዎች ከኢትዮ ኤፍ ኤም ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደተናገሩት፣ በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ስለድርቁ አሳሳቢነት ተገቢውን ያህል ትኩረት እየተሰጠው አይደለም ብለዋል፡፡
በመሆኑም አሁን ዋና ትኩረት መሆን ለዜጎች እና ምንም ለማያውቁት እንስሳት የምንደርስበትና ህይወት የምንታደግበት ሰአት መሆኑ አጽንኦት ሊሰጠው እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡
በሔኖክ ወ/ገብርኤል
የካቲት 17 ቀን 2015 ዓ.ም
ለተጨማሪ መረጃዎች የቴሌግራምና የዩቲዩብ ቻናሎቻችንን ይቀላቀሉ!
Telegram https://t.me/ethiofm107dot8
YouTube https://www.youtube.com/@onelovebroadcast
ያሎትን አስተያየት እና ጥያቄ በአጭር መልዕክት 6321 ላይ ይላኩልን።
ከኛ ጋር ስለሆናችሁ ከልብ እናመሰግናለን።
Source: Link to the Post