
በራያ ቆቦ በመቶዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች በተለይም ወጣቶች ከቤታቸው እየታፈኑ ለእስር እና ለድብደባ እየተዳረጉ ነው፤ ከቤታቸው የወሰዷቸውን ወጣቶች የተማረኩ ፋኖዎች በሚል ዶክሜንታሪ ሊሰሩባቸው መሆኑን ምንጮች ተናግረዋል። አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ ሀምሌ 7/2015 ዓ/ም_አዲስ አበባ ኢትዮጵያ በሰሜን ወሎ ዞን ራያ ቆቦ እና አካባቢው በአካባቢው በተሰማራ የኦህዴድ ብልጽግና አገዛዝ ጦር አማካኝነት ሀምሌ 6/2015 ከጠዋት ጀምሮ ሙሉ ቀን ተኩስ የተከፈተበት መሆኑ ይታወቃል። በዚህ በምስራቅ አማራ ፋኖዎች እና በነዋሪዎች ላይ በተከፈተው ተኩስም በርካታ ንጹሃን ወገኖች መገደላቸውና መቁሰላቸውን አሚማ ከሆስፒታል ምንጮች ያገኘው መረጃ አመልክቷል። በጤና ተቋማትም እየቆሰሉ እየተወሰዱ ያሉት ምንም የማያውቁ ህጻናት ሲሆኑ በርካቶች ሲሞቱ የተወሰኑት የህክምና ትብብር እየተደገገላቸው ነው ተብሏል። የጤና ባለሙያዎቹም በሚተኪሰው ከባድ መሳሪያ ድምጽ በመረበሽ የህክምና ስራቸውን በተገቢ ሁኔታ ለመስራት መቸገራቸውን ገልጸዋል። በመቶዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች በተለይም ወጣቶች ከቤታቸው እየታፈኑ ለእስር እና ለድብደባ እየተዳረጉ መሆኑም ተነግሯል። ከቤታቸው አፍነው የወሰዳቸውን ወጣቶችም የተማረኩ ፋኖዎች በሚል ዶክሜንታሪ ሊሰሩባቸው ስለመሆኑ ምንጮች ተናግረዋል። አሚማ ቆቦ እና አካባቢው እንዴት ሆኖ እንዳደረ ሀምሌ 7/2015 ያነጋገራቸው ነዋሪዎች እንደሚሉት አገዛዙ ለግድያ እና ለአፈና ባሰማራው ጦር እና ከህዝቡ ፍላጎት እና የህልውና ትግል በተቃርኖ በመሰለፍ ለገዥው ባደሩ የፖሊስ አባላት የመንቀሳቀስ መብታቸው ተገድቧል፤ በየቤቱ እየገቡ የሚፈልጉትን እያፈኑ ወስደዋል፤ የሚገድሉትን ገድለዋል፤ የቆሰሉም በርካቶች ናቸው ሲሉ አክለዋል። ሀምሌ 6/2015 ለአገዛዙ አድረው በሰላማዊ ነዋሪዎች ላይ እንዲሁም ካራምቡላ ሲጫወቱ በነበሩ የቆቦ ልጆች ላይ ተኩሰው ግድያ የፈጸሙ የፖሊስ አባላት እንዳሉ ተገልጧል። ሀምሌ 5/2015 ምሽት ላይ ወደ ቤቷ አልፋ ስትሄድ የነበረች በአንዲት እናት ላይ ተኩሰው አሳዛኝ ግድያ መፈጸማቸውንም አውስተዋል። ነዋሪዎችን በስልክ እያነጋገርን ሳለም የከባድ መሳሪያ ድምጽ ሰምተናል፤ ከወልድያ መስመር ከፍተኛ ቁጥር ያለው አፋኝ ጦር እየተጓጓዘ ወደ ቆቦ መግባቱም ታውቋል፤ የተወሰኑ አስከሬኖችን በማንሳት በየአብያተ ክርስቲያኑ ስርዓተ ቀብር እየፈጸሙ መሆናቸው ታውቋል። ነገር ግን አሁንም የመንቀሳቀስ መብታቸውም በአገዛዙ ጦር በመገደቡ የጦርነት ቀጠና በነበሩ አካባቢዎች የወደቀ አስከሬን እንኳ በአግባቡ አንስተው ስርዓተ ቀብር ለመፈጸም አለመቻላቸው ን ነዋሪዎች ነግረውናል። መላው የአማራ ፋኖ እና ህዝቡ ከጎናችን ሊሆን ይገባል፤ በተናጠል መሳደድ፣ መፈናቀል እና መገደል ይብቃን የሚል ጥሪ ቀርቧል። አማራ ሚዲያ ማዕከል (አሚማ) በራያ ቆቦ፣አራዱም ፣አሳመምቻ ፣ቀመሌ ተክለሃይማኖት ፣ጠዘጠዛ ፣ሮቢት እና ጎብዬ ዙርያ ባሉ አካባቢዎች በፋኖ እና በህዝብ ላይ የተጠናከረ ተኩስ መከፈቱን ተከትሎ የታቀደውን ጥቃት ለመመከት ብሎም ለመቀልበስ የምስራቅ አማራ ፋኖ ከህዝቡ ጎን በመሰለፍ ከፍተኛ ተጋድሎ እያደረገ መሆኑን የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ፋኖ አበበ ፈንታው መግለጹ እና መላው አማራ ከተናጠል ይልቅ የተናበበ የሞት ሽረት ትግል እንዲያደርግ ጥሪ ማድረጉ ይታወሳል። አሚማ ከራያ ቆቦ ነዋሪዎች ጋር ያደረገውን ቆይታ በዩቱዩብ አድራሻው የሚያጋራ ይሆናል።
Source: Link to the Post