
በቋራ ወረዳ ከሰሞኑ ተከስቷል የተባለውን የአጣዳፊ ተቅማጥ እና ትውከት (አተት) በሽታን በተመለከተ ተገቢ ትኩረት አልተሰጠም ሲሉ በለይቶ ማቆያ ት/ቤት ግቢ ውስጥ ያሉ ህሙማን ተናገሩ፤ የዘርፉ ባለሙያዎች ወገናዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ተጠይቋል። አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ ሀምሌ 10/2015 ዓ/ም_አዲስ አበባ ኢትዮጵያ በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በርሚል ከተባለ ዘካባቢ ከሰሞኑ ተከስቷል የተባለውን የአጣዳፊ ተቅማጥ እና ትውከት (አተት) በሽታን በተመለከተ ተገቢ ትኩረት ባለመሰጠቱ የሰው ህይወት እየጠፋ እና የህሙማንም ቁጥር እየጨመረ ስለመሆኑ ተገልጧል። ይህን ቅሬታ ለአሚማ ያቀረቡት ለይቶ ማቆያ በሚል በቋራ ሀይ ስኩል ግቢ ውስጥ ያሉ ህሙማን እና ለምርመራ በሚል እንዲገቡ እና ሾልከው በመውጣት ከሌሎች ጋር እንዳይቀላቀሉ በጸጥታ አካላት የሚጠበቁ ናቸው። ምልክቱ ከታዬባቸው እና ለማጣራት በሚል በቋራ ሀይ ስኩል ተለይተው እንዲቀመጡ ከተደረጉት ህሙማን መካከል የቀረበው ቅሬታ:_ ከበርሚል አካባቢ ወደ ገለጉ ስንመለስ ከተገኘን ተይዘን ወደ ማዕከል እንድንገባ ይደረጋል። በሽህ የሚቆጠርን ህዝብ በአንድ ቦታ ዘግቶ ከማስቀመጥ ያለፈ ኦአርኤስን ጨምሮ አስፈላጊ የሆነ የህክምና ግብአት እና እርዳታ እየተሰጠን አይደለም። ሀምሌ 7/2015 ከታመሙት ሰዎች መካከል የተወሰኑት ሰዎች ህይወታቸው አልፏል። የሰው ህይወት እየጠፋ መሆኑ እየታወቀ እንኳ ስለምን በቂ ትኩረት እንደማይሰጠው አይገባንም ሲሉ ተናግረዋል። የጉዳዩን አሳሳቢነት በተመለከተ አሚማ ያነጋገረው የሆስፒታል ጤና ባለሙያ:_ ከሀምሌ 7/2015 ጀምሮ የተከሰተ በሽታ ነው፤ በመጀመሪያው አንድ ቀን ወደ ቋራ ሆስፒታል 75 ታካሚዎች የገቡ ሲሆን ተቅማጥ እና ትውከት ይታይባቸው ነበር። በዚህም በክሊኒካል ደረጃ አተት ስለመከሰቱ ታምኖበት እየተሰራ ነው። በላብራቶሪ ደረጃ ግን እስካሁን ይሄ ነው የሚል የተረጋገጠ እና የተገለጸ ነገር አልሰማንም። በመቀጠል ግን ወደ ቋራ ሀይ ስኩል በመውሰድ እንደ ለይቶ ማቆያ አድርገው ምልክቱ የሚታይባቸውን ሰዎች እየሰበሰቡ መሆኑ ተገልጧል። በየቀኑ የሚገባው ሰው ቁጥር እየጨመረ ነው። የኦአርኤስ (Oral rehydration therapy_ORS) እጥረት እያጋጠመ ነው። የቀረበ ጥሪ:_ ከወረዳ እስከ ዞን እና ክልል ድረስ የሚመለከተው በተለይም የዘርፉ ባለሙያዎች ኃላፊነታቸውን ይወጡ። ወዲያውኑ ላብራቶሪ ተሰርቶ የበሽታው ምንነት ተለይቶ መሰረት ነበረበት፤ የምግብ፣ የውሃ፣ የመድኃኒትና መሰል የግብአት እጥረት ፈጽሞ ሊያጋጥም አይገባም። የሰው ኃይል፣ የአቅርቦት እና የትራንስፖርት ችግር ሊያጋጥም አይገባም። በአስቸኳይ የሁሉም አካላት የተናበበ ርብርብ ርብርብ ያስፈልጋል። ብዙ ጉዳት ከመድረሱ በፊት በአፋጣኝ በቁጥጥር ስር እንዲውል መስራት የግድ ይላል። ከቋራ ሆስፒታል ውጭ ሞት የተመዘገበ ስለመሆኑ መረጃ እንዳላቸውም ባለሙያዎቹ ተናግረዋል። በመጨረሻም የምናወራው ስለ ህይወት ስለሆነ ሁሉም አካላት የድርሻቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ እና አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ የሚል ጥሪ ቀርቧል። በምዕ/ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በርሚል አካባቢ የኮሌራ መሠል ወረርሽኝ ተነስቶ የሞት እና ሕመም አደጋ እያስከተለ ከመሆኑም በተጨማሪ በማዕ/ጎንደር ዞን አለፋ ወረዳ ከቦታው የመጡ 6 ሙሉ ምልክቱን ያሳዩ ሰዎች በአሁኑ ሰዓት ሻሑራ ሆስፒታል ተኝተው በመታከም ላይ መሆኑን በመጥቀስ ምልክቱን ያሳዩ ሕሙማን ሲታዩ ኅብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግና በጤና ተቋም ሲመጡም ከሌሎች መጠይቆች ባሻገር የጉዞ ታሪክ መኖራቸውን ማረጋገጥና አስፈላጊውን ሕክምናና ጥንቃቄ እንዲደረግ ሲል የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ጤና መምሪያ ማሳሰቡንም ለማወቅ ተችሏል።
Source: Link to the Post