በናይጄሪያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የገዢው ፓርቲ እጩ አሸነፉ

https://gdb.voanews.com/b1f2830e-aa88-44f0-9418-c8b8644e2cf5_w800_h450.jpg

በናይጄሪያ ባለፈው ቅዳሜ በተደረገው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የገዢው ፓርቲ እጩ የሆኑት ቦላ አህመድ ቲኑቡ አሸንፈዋል ሲል የአገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ዛሬ አስታውቋል፡፡

የተቃዋሚ ፓርቲ እጩዎቹ ግን ምርጫው ማጭበርበርና ቴክኒካዊ ችግር ስለነበረበት በድጋሚ ድምጽ እንዲሰጥ ጠይቀዋል፡፡

ቦላ አህመድ ቲኑቡ 8.8 ሚሊዮን ድምጽ በማግኘት ፕሬዚዳንት ሆነው መመረጣቸውን የምርጫ ኮሚሽኑ ሊቀመንበር ማሃሙድ ያኩቡ በአገሪቱ ብሄራዊ ቴሌቪዥን ማስታወቃቸውን የቪኦኤው ቲመቲ ኦቢይዙ ከአቡጃ ከላከው ዘገባ ማወቅ ተችሏል፡፡

የቲቡኑ ዋናው ተፎካካሪ የነበሩት የቀድሞ ምክትል ፕሬዚዳንት አቲኩ አቡባካር 7 ሚሊዮን ድምጽ ሲያገኙ፣ የሠራተኛ ፓርቲው ፒተር ኦቢ 6 ሚሊዮን ድምጽ አግኝተዋል፡፡

በናይጄሪያ ዲሞክራሲያዊ ታሪክ ከፍተኛ ፉክክር የታየበት ነበር በተባለው ምርጫ የአገሪቱ የኢኮኖሚ መዲና የሆነችው ሌጎስ የቀድሞ አገረ ግዢ ቲኑቡ ፕሬዚዳንት ሆነው ተመርጠዋል፡፡ የ70 ዓመቱ ቲኑቡ የፖለቲካ ‘የነፍስ አባት’ በመባል ሲታወቁ፣ ውጤቱን ተከትሎ ባደረጉት ንግግር ተቃዋሚዎችን ጨምሮ ሁሉም ናይጄሩያውያን ለአገሪቱ ሲሉ በአንድነት እንዲቆሙ ጥሪ አድርገዋል፡፡

የቴክኒክ ችግር ተከስቶ ነበር እንዲሁም በመራጮች ላይ ጫና ተደርጓል፣ ድምጽም ተጭበርብሯል በሚል የተቃዋሚ እጩዎቹ ጉዳዩን በፍርድ ቤት እንደሚሞግቱት አስታውቀዋል፡፡

Source: Link to the Post

Leave a Reply