በአዲስ አበባ አንድ እቁላል ከ14 ብር እስከ 16 ብር እየተሸጠ ነው፡፡
‹‹ለእንቁላል ጣይ ዶሮ መኖ በኩንታል ከ 3 ሺህ 680 እስከ 4 ሺህ ብር ወጪ እያስደረገን ነው››— የኢትዮጵያ ዶሮ አርቢዎች እና አቀናባሪዎች ማህበር
በመኖ መወደድ እና ከዚህ ቀደም ተከስቶ በነበረው ወረርሺኝ ምክንያት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዶሮዎች መሞታቸው አብዛኛው ዶሮ አርቢ አባላትን ዘርፉ ውስጥ እንዳይቆዩ እያደረጋቸው መሆኑ ተገልጧል፡፡
ይህን ያለው የኢትዮጵያ ዶሮ አርቢዎች እና አቀናባሪዎች ማህበር ነው፡፡
የማህበሩ ምክትል ሃላፊ አቶ ቴዎድሮስ ካሳሁን ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንደተናገሩት፣የመኖው መወደድ የእንቁላል ዋጋ ከዚህም በላይ ከፍ እንዲል ሊያደርገው እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸውልናል፡፡
ኢትዮ ኤፍ ኤም ባደረገው ቅኝት በአማካይ የ1 እንቁላል ዋጋ ከ 14 ብር አስከ 16 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
አንድ እንቁላል ጣይ ዶሮ ከምታስገኘው ገቢ 75 ከመቶዋ ወጪዋ መሆኑን አቶ ቴዎድሮስ ነግረውናል፡፡
አቶ ቴዎድሮስ ጨምረውም ቀደም ሲል ” ዶሮ እና የዶሮ ውጤቶችን ያለ ስጋት መጠቀም ይቻላል ” የሚል ትዕዛዝ አስከተሰጥበት ቀን ድረስ በነበረው ጊዜ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዶሮዎች መቀበራቸውን እና ብዙ አርቢዎችም ላይ ኪሳራ ማስከተሉን ነግርውናል፡፡
በማህበሩ ውስጥ በአሁኑ ሰዓት 125 አርቢ አባላት መኖራቸውንም ሰምተናል፡፡
ዘርፉ በባንክ በብድር ቢደገፍ ፣ እውቀቱ እና ማምረቻ ቦታው ለወጣቶች በመስጠት ቢታገዝ ፣ ገበሬው ደግሞ በማርባቱ ሂደት በብዛት ቢቀላቀል መሻሻል ሊኖረው ይችላልም ብለዋል፡፡
በረድኤት ገበየሁ
ግንቦት 10 ቀን 2015 ዓ.ም