
በእነ መላክ ምሳሌ መዝገብ፣ ከ20 ሰዎች መካከል ቅድስት ከበደ የተባለች ሴት ብቻ በ50 ሽህ ብር ዋስትና ከእስር እንድትፈታ በችሎቱ ተወስኗል። አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ ሀምሌ 17/2015 ዓ/ም_አዲስ አበባ ኢትዮጵያ በእነ መላክ ምሳሌ መዝገብ፣ 20 ሰዎች ሀምሌ 17/2015 ከሰዓት በኋላ በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት 1ኛ ጸረ ሽብር ችሎት ቀርበው ነበር። ፍ/ቤቱ “የዐቃቢ ህግ ጠርጥሬያቸዋለሁ ብሎ ካቀረበው የወንጀል አፈጻጸም እና አሁን ካለው የሀገሪቷ ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ዋስትናቸውን አክብረው ይመጣሉ ብለን አናምንም” በማለት ከ17ተኛ ተከሳሽ ውጭ ሌሎች 19 ሰዎችን የዋስትና መብታቸውን ከልክሏል ሲል ጠበቃ ቴዎድሮስ ገልጧል። ባልተለመደ መልኩ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የፌደራል ፖሊስ እስረኞችን አጅቦ የተገኘ ሲሆን ይህም በእነ ዶ/ር ወንዶሰን መዝገብ እንደተደረገው “አማራነት ይቀነቀናል” የሚል ስጋት ስላለው ሊሆን እንደሚችል ተመላክቷል። የእለቱ ችሎት ተጠናቆ ከአዳራሹ ሲወጡም ቤተሰቦች እና የችሎት ታዳሚዎች በጭብጨባ ሞራል በመስጠት ነበር የተሰናበቷቸው። እስረኞቹ ከሀምሌ 17/2015 ጀምረው ወደ ማ/ቤት እንዲወርዱ ታዟል። ለሀምሌ 20/2015 እንዲቀርቡም ተለዋጭ ቀጠሮ መሰጠቱ ታውቋል። ፍ/ቤቱ 17ተኛ ተከሳሽ የሆነችውን የወ/ሮ ቅድስት ከበደን በ50 ሽህ ብር ዋስትና ከእስር እንድትፈታ ትዕዛዝ መስጠቱ ተገልጧል። ቅድስት ከበደ ሰብስቤ ከአሁን ቀደም ለሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኢሰመኮ የሚከተለውን የሰብአዊ መብት ጥሰት አቅርባ ነበር። ሚያዚያ 27 ቀን 2015 ዓ.ም ምሽት 1፡30 ሰዓት ከአዲስ አበባ አፍነው ወስደውኝ ገላን በሚባል ቦታ ታፍኜ ቆይቻለሁ፡፡ ከተያዝኩ በኋላ አስከ 18/9/2015 ዓ.ም ገላን ማጎሪያ ቤት ውስጥ ቆይቻለሁ፡፡ በቆይታዬ ከፍተኛ ሆነ ሰብዓዊ መብት ጥሰት አድርሰውብኛል፡፡ 3 (ሶስት) ቀን ያለ ምግብ እንድቀመጥ አድርገውኛል፡፡ ወገቤን መትተውኝ በዚህ ምክንያት 13 ቀን ደም እንደ ውኃ ሲፈሰኝ ነበር።… ለ22 ቀናት ያህል ብቻዬን ሴት እስረኛ በሌለበት ቆሻሻ ቤት ውስጥ ከአይጥ ጋር በማስቀመጥ አስረውኛል፡፡ በድብደባው የተነሳ ማህጸኔ ስለተጎዳ እና በጣም የህመም ስሜት ስለሚሰማኝ የማስታገሻ መድኃኒት እየወሰድኩ ነው፡፡ ከወንድ እስረኞች ጋር ሽንት ቤት እንድጠቀም አድርገውኛል፡፡ በጊዜው እነዚህ ሰዎች ሲይዙኝ/ስያዝ ሳምሰንግ ሞባይል ስልክ፣ ሽጉጥ ከ8 ጥይት ጋር፣ ፓስፖርት እና መንጃ ፈቃድ የወሰዱብኝ ሲሆን አሁን የት እንዳሉም አላውቅም፡፡
Source: Link to the Post