
በደቡብ ጎንደር ዞን በአንዳቤት ወረዳ መነሻቸውን ከአምስት ቀበሌዎች ያደረጉ አርሶ አደሮች የአፈር ማዳበሪያ የአቅርቦት ችግር እንዲቀረፍ በሰላማዊ መንገድ ወረዳውን ቢጠይቁም ከመጉላላት ያለፈ ተገቢ ምላሽ አለማግኘታቸው ተገለጸ፤ የሚዲያ ተቋማት ያለመሰልቸት ለገበሬው ድምጽ እንዲሆኑ ተጠይቋል። አማራ ሚዲያ ማዕከል (አሚማ) ሀምሌ 5/2015 ዓ/ም_ አዲስ አበባ ኢትዮጵያ በደቡብ ጎንደር ዞን በአንዳቤት ወረዳ መነሻቸውን ከአምስት ቀበሌዎች ያደረጉ አርሶ አደሮች የአፈር ማዳበሪያ የአቅርቦት ችግር እንዲቀረፍላቸው ሀምሌ 3/2015 በሰላማዊ መንገድ ወረዳውን ቢጠይቁም ከመጉላላት ያለፈ ተገቢ ምላሽ አለማግኘታቸውን በመግለጽ የሚዲያ ተቋማት እየተሰራ ያለውን የኢኮኖሚ አሻጥር በማውገዝ ያለመሰልቸት ለገበሬው ድምጽ እንዲሆኑ ተጠይቋል። በደቡብ ጎንደር ዞን በአንዳቤት ወረዳ የሚኖሩ ከ5 ቀበሌዎች ማለትም:_ 1) ከጎጣ ቀበሌ፣ 2) ከግሸና ቀበሌ፣ የ 3) ከትክል ድንጋይ፣ 4) ከስሜት ሾላየ እና 5) ከአዳማ ቀበሌዎች ወደ ወረዳ ጅራፋቸውን ጠቅልለው ሆ! ብለው በሰላማዊ ሰልፍ ተሰልፈው በመምጣት መጥቶ ለወረዳው የመንግስት አካላት ብሶታቸውን ማሰማታቸው ይታወሳል። የመረጃ ምንጫችን እንደሚሉት ካነሷቸው አንኳር ጥያቄዎች መካከልም:_ 1) በማዳበሪያ እጥረት ምክንያት መሬታችን ጦም እያደረ ነው። ከ40 እስከ 50 ኬሻ የአፈር ማዳበሪያ ሲጠቀም የቆዬ አርሶ አደር አሁን ላይ በልመና እየወሰደ ያለው ከፍተኛው ከ3 እስከ 5 ኬሻ ብቻ ነው። 2) የፍታሃዊነት ችግር አለ። እጥረቱ እንዳለ ሆኖ የወረዳ እና የቀበሌ አመራሮች በመመሳጠር፣ በመጠጥ እና በጠላ እየታለሉ፣ በሙስና ለዘመድ አዝማድ እየተገዙ ነው የሚሰጡ። ማዳበሪያ በጨለማ በኮንትሮባንድ አንድ ኬሻ እስከ 1,900 ብር ገዝተው 6,000 ብር፤ አንድ ኩንታል 4,000 ብር ገዝተው 12,000 ብር እየሸጡ ድሃው አርሶ አደር ጦም እያደረ ነው ብለዋል። 3) የአንዳቤት ነዋሪ በአብዛኛው ጤፍ አምራች አርሶ አደር በመሆኑ፣ እንደአብነትም አንድ አርሶ አደር ከ100 እስከ 150 ኩንታል ጤፍ በማምረት የሚታወቅ ቢሆንም አሁን ላይ ያለ ማደበሪያ ካልተዘራ ግን 10 ኩንታል እንኳ ለማግኘት ከባድ ነው ሲሉ የጉዳቱን መጠን ጠቁመዋል። በተለይም የቀበሌ አመራሩ ሽጦ በልቶናል፤ እስከ ዞን እና ክልል ድረስ በመሄድ እየጮህን እንሞታለን። የሰሚ ያለህ ጤፋችን ሽጠን ከጨረስን በኋላ ማደበሪያ የለም። ለምን? ቀድማችሁ ብትነግሩን ጤፋችን አንሸጥም ነበር? የሚል ሀሳብ ተነስቷል። ጭራሽ ማደበሪያ ያልደረሰው አርሶ አደርም አለ። 50% የሚሆነው የአርሶ አደር መሬት ሳይዘራ የሚከርም ነው፤ በአስቸኳይ መፍትሄ ካልተሰጠው…ለዛውም በሰኔ ካልደረሰ ምን ያደርግለታል? የሚል ቁጣውን አሰምቷል። ነገር ግን አሁንም ከመጉላላት ያለፈ ከካድሪው የተሰጠው ምላሽ ችግሩን የሚፈታ እንዳልሆነ በመግለጽ ችግሩ እንደ ወረዳ፣ ዞንና ክልል አማራን በኢኮኖሚ የማዳከም ሸፍጥ ስለሆነ የሚዲያ ተቋማት ሳትሰለቹ ለገበሬው ድምጽ ብትሆኑ የሚል ጥሪ ቀርቧል። ይህ የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት ጥያቄ በተለያዩ የአማራ አካባቢዎች በልዩ ልዩ መልኩ እየቀረበ ቢሆንም ተገቢ ምላሽ እያገኘ አለመሆኑ ግልጽ ነው።
Source: Link to the Post