ቻይና ከጁዋን ሳተላይት ጣቢያ ማዕከል ሶስት ጠፈርተኞችን ወደ አዲስ የጠፈር ጣቢያ እንደላከች እና ለሶስት ወራትም በሕዋ ላይ እንደሚቆዩ አስታውቃለች፡፡አዲሱን የጠፈር ጣቢያዬን ለማጠናቀቅ አንድ እርምጃ ቀርቶኛል ያለችው ቻይና ሶስቱ ጠፈርተኞቼ በተሳካ ሁኔታ ወደ ቦታው ደርሰዋል ብላለች፡፡
ቻይና ቲዮንጎንግ ወይም የሰማዩ ቤተ-መንግስት በማለት የምትጠራው አዲሱ የጠፈር ጣቢያዋ ተመራማሪዎቼ በምሕዋሩ ቆይታቸው ብዙ ጥናት እንደሚያደርጉ ላሳውቅ እወዳለሁ ብላለች፡፡የቻይና የጠፈር ምርምር ኤጀንሲ ከዚህ ቀደም ወደ ሕዋ ባደረገው ተልዕኮ ስኬታማ እንደነበር በማስታወስ ቻይና የራሷን የጠፈር ጣቢያ ማቋቋም እንዳስፈለጋት አንስቷል፡፡
የዓለም ዓቀፉ የጠፈር ጣቢያ አይ ኤስ ኤስ በበኩሉ 19 ሀገራት እና 200 የጠፈር ተመራማሪዎችን በአባልነት ቢያቅፍም ቻይናን ግን ከማሕበሩ ውስጥ እንዳላካተተ አሳውቋል፡፡ቻይናም በዓለም ዓቀፉ የጠፈር ጣቢያ ከአሜሪካ ጋር ባለኝ የሻከረ ግንኙነት የተነሳ በአባልነት ባልመዘገብም የራሴን ጣቢያ ማቋቋም እንደምችል አሳያለሁ ብላለች፡፡
ዘገባው፡- የፍራንስ 24 ነው
ቀን 10/10/2013
አሐዱ ራድዮ 94.3
The post ቻይና ሶስት የጠፈር ተመራማሪዎችን ወደ አዲስ የጠፈር ጣብያ መላኳን አስታወቀች፡፡ appeared first on አሐዱ ራድዮ 94.3 እና ቴሌቪዥን.
Source: Link to the Post