
“አልሸማቀቅም፤ እንደዚህ ዓይነት ነገሮች እኔን አይሰብሩኝም!” ጋዜጠኛ፣ መምህርት እና ጸሀፊ መስከረም አበራ በችሎት የተናገረችው አማራ ሚዲያ ማዕከል (አሚማ) ሀምሌ 3/2015 ዓ/ም_ አዲስ አበባ ኢትዮጵያ በእነ ዶ/ር ወንዶሰን አሰፋ መዝገብ ሶስቱ ጋዜጠኞች_መስከረም አበራ፣ ጎበዜ ሲሳይ እና ዳዊት በጋሻው ምን አሉ? በእነ ዶ/ር ወንዶሰን አሰፋ 51 ሰዎች በተከሰሱበት መዝገብ ሶስቱ ጋዜጠኞች_መስከረም አበራ፣ ጎበዜ ሲሳይ እና ዳዊት በጋሻው ሀምሌ 3/2015 በተካሄደው ችሎት ስለተናገሩት ጉዳይ አሚማ ከጠበቃ ሄኖክ አክሊሉ ጋር ካደረገው ቆይታ የተረዳውን በሚከተለው መልኩ ለማጋራት ወዷል። (1) ጋዜጠኛ፣ መምህርት እና ጸሀፊ መስከረም አበራ በችሎቱ ምን አለች? የፍ/ቤቱን እንቅስቃሴ በጥርጣሬ እንደምታዬው፣ የአማራ ህዝብ ከ1983 ዓ/ም ጀምሮ ከፍተኛ በደል በመንግስት እየደረሰበት እንደሆነ፣ አማራ ጠል ስርዓት ነው በአገሪቱ ያለው። አማራ እየተጨፈጨፈ ነው። እኛም ከዚህ ተከሰን የቀረብ ነው የአማራ ህዝብ ጠበቃ በመሆናችን ነው። እናም ድምጻችን ተዘግቶ ሊፈረድብን ነው ይህ እየተካሄደ ያለው። የአማራን ህዝብ መሪ አልባ የማድረግ ጉዳይ ነው። ነገር ግን በመከሰሴ ለልጆቼ የምነግረው የምኮራበት ታሪክ ነው ያለው የማፍረው ምንም ዓይነት ነገር የለም። አልሸማቀቅም፤ እንደዚህ ዓይነት ነገሮች እኔን አይሰብሩኝም! በማለት በችሎቱ ካልተሰራው ስራ እና ከተቀየሩት ዳኛ ጋር በተያያዘ የተሰማትን ስሜት ገልጻለች። ለምንድን ነው ዛሬ ብይን ያልተሰጠው? ለምንስ ነው አላግባብ ዳኛ እንዲቀዬር የተደረገው? ስትል ስሜቷን ለችሎቱ ገልጻለች። (2) ጋዜጠኛ ጎበዜ ሲሳይ:_ “ስታሰር ጀምሮ ያሰረኝ ፖሊስ ዳኛውም እኛ ነን፤ ዐቃቢ ህጉም እኛ ነን ይለኝ ነበር፤ ንቄ ትቼው ነበር። እኛ ነን የሚለው ግን አሁን ሚዛን እየደፋብኝ ነው ያለው።” በማለት በተለይም የፍ/ቤቱ አስተዳደር ዳኞችን አላግባብ መቀዬሩ ጋር በተገናኘ ተመሳሳይ ነገር ከዚህ በፊት የተባለውን እሱን የሚገልጽለት፣ ትክክል መሆኑን የሚያሳይለት ነገር መሆኑን እንዳዬ ለፍ/ቤቱ ገልጧል። ስለዚህ ለምንድን ነው ይህ የሚደረገው ሲል መረር ባለ ሁኔታ ስሜቱን ገልጧል። (3) ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው:_ በመንግስት የመገናኛ ብዙሃን እና በፓርቲ ሚዲያዎች የተዘገበው ዘገባ ነጻ ሆነው የመገመት መብታቸውን የሚጥስ እና የሚጎዳ ነው በሚል በቀረበው አቤቱታ ላይ ለተቋማቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር። ኢሰመኮ ባለፈው ቀጠሮ ባይቀርብም ከቀጠሮው በኋላ ቀርቦ የሰብአዊ መብት አኳያ የቀረበውን አቤቱታ በተመለከተ በምርመራ በማጣራት ለፍ/ቤቱ ሪፖርቱን ማያያዙን የገለጸው ችሎቱ ከሚቀጥለው ቀጠሮ በፊት ግልባጩን በመውሰድ ተገቢ የሚሉትን አስተያዬት እንዲሰጡበት ለጠበቆች ፈቅዷል። ከመገናኛ ብዙሃን አንጻር ግንኦቢኤን፣ ፋና ብሮድካስቲንግ ከዚህ በፊት መልስ ሰጥተዋል፤፣ ዋልታ፣ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን መልስ ሰጥተዋል። የሚዲያ ዘገባውን በተመለከተ ዶክሜንታሪ አልሰራንም በሚል ለፍ/ቤቱ የሰጡትን ምላሽ አስመልክቶ ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው የሚከተለውን አስተያዬት ሰጥቷል:_ ዶክሜንታሪ ሰርተዋል ሳይሆን በሚዲያ ዘገባቸው ላይ እኛን ወንጀለኛ ሊያደርግ በሚችል፣ ቤተሰቦቻችንን ሊያስደነግጥ በሚችል፣ ጓደኞቻችንን ላይ ተጽዕኖ ሊፈጥር በሚችል ሽብርተኛ አድርጎ የጋራ ግብረ ኃይሉን መግለጫ አውጥተዋል፤ ሚዛናዊነት በጎደለው ሁኔታ ዘግበዋል። ከአጠገባችን ቦንብ እና መሳሪያ አድርገው ፎቶአችንን እና ስማችንን አድርገው ዘግበዋል፤ ይህ ደግሞ አሁንም በእነዚህ ተቋማት አርካይብ ላይ የሚገኝ ስለሆነ ተጽዕኖ ያሳድርብናል ብለው ለፍ/ቤቱ ገልጸዋል። ፍ/ቤቱም ይህንን ጉዳይ አይቶ ተገቢ ነው የሚለውን ትዕዛዝ ለመስጠት ለቀጣይ ቀጠሮ አሻግሮታል። ከሰብአዊነት ጋር በተገናኘ ኮፒውን ወስደው አስተያዬት የሚሰጡበት መሆኑን ጠበቃ ሄኖክ ለአሚማ አስታውቋል። በአጠቃላይ እስረኞቹ በተደጋጋሚ በችሎት ሲቀርቡ ሲያንጸባርቋቸው ከነበሩ ጉዳዮች መካከልም:_ የፍትህ ስርዓቱ ላይ ጥርጣሬ እንዳላቸው፣ አማራ ጠል እንደሆነ ስርዓቱ፣ ሕገ መንግስቱ አማራ ጠል እንደሆነ፣ የዳኝነት ስርዓቱ በዚህ የተቀረጸ ስለመሆኑ በተደጋጋሚ ለፍ/ቤቱ የገለጹ፣ የህሊና እስረኛ በመሆናቸው እንጅ የታሰሩት ሰርቀው አለመሆኑን በተደጋጋሚ ለችሎቱ ይገልጹ እንደነበር፣ ችሎቱም ከገለልተኝነት አንጻር ምንም ዓይነት ስጋት አይግባችሁ ሲል ነው የነበረው ሲል ጠበቃ ሄኖክ አስታውሷል። አሁን በዛሬው ቀጠሮ ወሳኝ በነበረ ጉዳይ ላይ የፍ/ቤቱ አስተዳደር ስልጣን አለኝና የፈለገውን ዳኛ አንስቶ የፈለገውን ዳኛ ማስቀመጡ ችሎቱ በገለልተኝነት ያለ ሶስተኛ ወገን ጣልቃ ገብነት ነው ስራዎችን የሚሰራው የሚለውን ተከሳሾቹ እንዳያምኑ ሆነዋል። ይህንንም ለፍ/ቤቱ በግልጽ ገልጸዋል። ሶስተኛ ወገን እዚህ ችሎት ላይ ተጽዕኖ እየፈጠረ ነው፤ ለዚህም ማሳያው ዳኛ እንዲነሳ እየተደረገ ነው። እዚህ 51 ተከሳሾች ባለንበት መዝገብ ውስጥ 51ዱም ተከሳሾች አማራ ነን፤ ከዛ በተረፈ በሌሎች መዝገቦችም ያሉ ቢታዩ በሙሉ አማራ ናቸው እየተከሰሱ ያሉት። ወንጀላቸው ማንነት፣ አማራነት ነው። አማራነታቸው ነው ወንጀለኛ እያደረገ ያለው። ከዚህ በመነሳት ፍትህ አናገኝም እያሉ ለችሎቱ እየገለጹ፣ በችሎቱ የሚሆነው ነገር ደግሞ በእናንተ ሚዲያ እና በሌሎችም እየተስተጋባ ባለበት ሁኔታ የፍ/ቤቱ አስተዳደር ግልጽነት በጎደለው ሁኔታ፣ ተጠያቂነትን በማይፈጥር ሁኔታ ዳኞችን አንስቶ እኛ ዳኛ የማንሳት ስልጣን አለን የሚለው ተከሳሾች የፍትህ ስርዓቱን የበለጠ እንዳያምኑትና በቀጣይ በችሎቱና በተከሳሾች መካከል የሚኖረው ግንኙነት ጤነኛ እንዳይሆን የሚያደርገው ይመስለኛል። ይህንንም ዛሬ በነበረው ችሎት ለመገንዘብ ችያለሁ። ተከሳሾቹ ለፍ/ቤቱ በግልጽ አማርኛ ይህንን ነው ሲገልጹ የነበረው። በቀጣይ ችሎት ይህንን አሁን የተደረገው ነገር የማይታረም፣ እንደዚህ ዓይነት ነገሮች የማይታረሙ ከሆነ የፍ/ቤቱ ሂደት በአግባቡ ለመከታተል እንደሚቸገሩ ለፍ/ቤቱ ሲገልጹ ነበር። ስለዚህ ከዚህ አንጻር ተከሳሾች ያደረባቸው ጥርጣሬ ምክንያታዊ እንደሆነ ነው እኔ የተረዳሁትኝ፤ ከፍትህ አንጻር እየተደረገ ያለው በተለይም በፍ/ቤቱ የበላይ አስተዳደር ዳኞችን እንደፈለገ የመቀዬሩ ነገር በተከሳሾች ላይ ሊፈጥር የሚችለው ተጽዕኖ ከባድ ነውና ፍትህ አናገኝም ወደሚል ጥግ እየገፋቸው ይመስለኛል። ይህንን በማለታቸው ደግሞ ተገቢነት የሌለው ግንዛቤ ነው ከፍ/ቤቱ የያዙት ለማለት ይቸግረኛል ብሏል ጠበቃ ሄኖክ ከአሚማ ጋር በነበረው ቆይታ።
Source: Link to the Post