አቶ ግርማ የሺጥላን ጨምሮ አምስት ሰዎች በ“ኢ-መደበኛ ኃይሎች” መገደላቸውን የአማራ ክልል መንግስት አስታወቀ

የአማራ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላን ጨምሮ አምስት ሰዎች በ“ኢ-መደበኛ ኃይሎች” በደረሰባቸው ጥቃት መገደላቸውን የአማራ ክልል መንግስት አስታወቀ። እነዚህ ኃይሎች በአቶ ግርማ ቤተሰቦች እና የግል ጥበቃዎቻቸው ላይ ጥቃቱን የፈጸሙት፤ በሰሜን ሸዋ ዞን መንዝ ጓሳ አካባቢ መሆኑንም የክልሉ መንግስት ገልጿል።

የአማራ ክልል መንግስት ይህንን ያስታወቀው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የአቶ ግርማን ሞት ይፋ ካደረጉ ከአንድ ሰዓት በኋላ ባወጣው መግለጫ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለአቶ ግርማ ሞት ተጠያቂ ያደረጉት፤ “ሐሳብን በሐሳብ ማሸነፍ ያቃታቸው” እንዲሁም “ነውጠኛ ጽንፈኞች” ሲሉ የገለጿቸውን አካላት ነው። የአማራ ክልል መንግስት በበኩሉ ጥቃቱን የፈጸሙት “ኢ-መደበኛ” እና “የሽብር ስራ እየሰሩ ያሉ ኃይሎች” ናቸው ብሏል።

የክልሉ መንግስት በዚሁ መግለጫው፤ አቶ ግርማ ጥቃት የደረሰባቸው ዛሬ ሐሙስ ሚያዝያ 19፤ 2015 ከሰዓት በኋላ “የመንግስት እና የድርጅት ስራዎችን ሰርተው” ከመሃል ሜዳ ወደ ደብረ ብርሃን እየተጓዙ በነበረበት ወቅት መሆኑን አስታውቋል። አቶ ግርማ የተወለዱት በሰሜን ሸዋ ዞን በሚገኘው መሃል ሜዳ አካባቢ መሆኑን የግል ህይወት ታሪካቸው ያመለክታል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ዛሬ አመሻሽ ላይ ባወጡት መግለጫም፤ በአቶ ግርማ ላይ የተደረገው “አስነዋሪ እና አሰቃቂ ተግባር” የተፈጸመው፤ ተወልደው ባደጉበት አካባቢ እንደነበር ጠቅሰዋል።

የአማራ ብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊው ከመገደላቸው አንድ ቀን አስቀድሞ፤ በሰሜን ሸዋ ዞን በደብረ ብርሃን ከተማ የስራ ጉብኝት ማካሄዳቸው ተገልጾ ነበር። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር በትላንትናው ዕለት ባወጣው መረጃ፤ አቶ ግርማ ከከተማዋ ተቀዳሚ ከንቲባ አቶ ካሳሁን እምቢአለ እና ከሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመሆን በግንባታ ላይ ያሉ ፕሮጀክቶችን መመልከታቸውን በፎቶግራፍ አስደግፎ አሳይቶ ነበር። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

[በዚህ ዘገባ ላይ ከቆይታ በኋላ ተጨማሪ መረጃ ታክሎበታል]

The post አቶ ግርማ የሺጥላን ጨምሮ አምስት ሰዎች በ“ኢ-መደበኛ ኃይሎች” መገደላቸውን የአማራ ክልል መንግስት አስታወቀ appeared first on Ethiopia Insider.

Source: Link to the Post

Leave a Reply