
እንስራ የተሰኘው ይህ ማጣመሪያ የስራ ማፈላለጊያ ዘዴ ሲሆን ትሬድ ኢትዮጵያ ኮሚሽኒንግ ከ Mercy Corps ሊዌይ ጋር በመተባበር ይፋ አድርጎታል።
ይህ የስራ ማጣመሪያ በድህረገፅ፣ በሞባይል መተግበሪያ ፣ በጥሪ ማዕከል ፣ በየወረዳው በሚቀመጡ ተንቀሳቃሽ ጆብ ኮርነር ሱቆች የታገዘ በየትኛውም የክህሎት ደረጃ ያሉ ስራ ፈላጊዎች ከስራ ቀጣሪዎችና ደላሎች ጋር የሚገናኙበት እንደሆነ ተገልጿል።
በመዲናይቱ ያሉ አሰሪና ሰራተኛ ድርጅቶች አቅም አነስተኛ መሆን አብዛኞቹ ድርጅቶች የቤት ሰራተኛ እና አሰሪ ብቻ በማገናኘት ላይ በመሆናቸውይህንን የስራ ማጣመሪያ ለመስራት እና ወደተግባር ለመግባት ማስፈለጉን የትሬድ ኢትዮጵያ ኮሚሽኒንግ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ በርናባስ ወልደገብርኤል ተናግረዋል።
ዳይሬክተሩ በቀጣሪ እና ተቀጣሪ መሀከል የተአማኒነት ጉዳይ፣ ለስራ አገናኞች የሚከፈል ክፍያ ፣የክህሎት እና ስራው አለመመጣጠን ፣ የቦታና የጊዜ ውስንነት እና ከመንግስት ጋር በተያያዘ የህጋዊነት ጉዳይ የሚሉትም የስራ ማጣመሪያውን ለመጀመር ምክንያቶች እንደነበሩ አክለው ገልፀዋል።
የስራ ማጣመሪያው ለስራና ሰራተኛ አገናኝ ደላሎችም እንዲገለገሉበት የተሰራ ሲሆን ስራቸውን የሚያቀላጥፍ እና ገቢያቸውንም የሚያሳድግ ነው ተብሏል።
በአዲስአበባ አጠቃላይ የስራ አጥ ብዛት 20 በመቶ ሲሆን ፣ ከነዚህም ውስጥ ከ 15-29 አመት ያሉ ወጣት ስራ አጦች ብዛት 24 በመቶ የሚሆነውን እንደሚይዝ ተገልጿል።
እስከዳር ግርማ
መጋቢት 08 ቀን 2014 ዓ.ም
Source: Link to the Post