ኢትስዊች አ.ማ. የዲጂታል ክፍያ ግብይቶችን ለማሳደግ የሚያስችለውን ተጨማሪ ካፒታል አጸደቀ፡፡
የኢትስዊች አ.ማ. ሊቀመንበር አቶ ሰለሞን ደስታ እንደገለፁት፣የጸደቀዉ ተጨማሪ ካፒታል ኩባንያውን ለመቀላቀል ፍላጎት ያላቸውን አዲስ የሚመጡ ባንኮች ለማካተት የሚያስችል ነዉ፡፡
በተጨማሪም የነባር ባለአክሲዮኖች የጋራ መሠረተ ልማት ተጠቃሚነትን እና የዲጂታል ክፍያ ግብይቶችን ለማሳደግ ያለመ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡
ማህበሩ የአምስት ዓመት ስትራቴጂውን በሀገር አቀፍ ደረጃ በተቀመጠው ክፍያን የማዘመን ሂደት ጋር በማስተሳሰር በፖሊሲ ዘርፍ፣ በገቢ ማስገኛ እንዲሁም በኦፕሬሽን ሥራዎች ላይ ከፍተኛ ስኬት እያስመዘገበ የሚገኝ ኩባንያ ነው ብለዋል፡፡
ኩባንያው በሁሉም አባል የፋይናንስ ተቋማት አቅምን በማጎልበት አስተማማኝ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል የስትራቴጂ ለውጦችን አድርጓልም ነው ያሉት፡፡
ውይይት የተደረገበት የካፒታል ጭማሪ በንግድ ሕጉ እና በብሔራዊ ባንክ መመሪያ መሠረት የተዘጋጀ መሆኑም ታዉቋል፡፡
አዲስ የፀደቀዉ በጀት የኩባንያውን ካፒታል ወደ ብር 3 ነጥብ 017 ቢሊዮን በላይ የሚያሳድግ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
እ.ኤ.አ. በ2011 የተቋቋመው ኢትስዊች የአክሲዮን ማህበር በሁሉም ባንኮች እና በኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ በርካታ ማይክሮፋይናንስ ድርጅቶች ባለቤትነት የተያዘ መሆኑን ኢትዮ ኤፍ ኤም ሰምቷል፡፡
ከ2016 ጀምሮ በሁሉም ባንኮች የሚሰሩ የኤቲኤም እና የPOS መሳሪይዎች ተናባቢነት እንዲኖርም አስችሏል።
በአባቱ መረቀ
መጋቢት 11 ቀን 2015 ዓ.ም