
ከአማራ ተማሪዎች ማህበር/አተማ/ በወቅታዊ የማህበሩ ሁናቴና የወደፊት የትግል አቅጣጫዎች ዙሪያ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ:- የካቲት 22 ቀን 2015 ዓ.ም አሻራ ሚዲያ ፣ *********************** የአማራ ሕዝብ ለብዙ አመታት ሕዝባዊ ህልዉናዉን በሚፈታተኑ የጠላቶቹ የወጥመድ እቅዶች ና ጥልፍልፎች ዉስጥ ሲያልፍ ለብዙ አመታት በሰነድ ተደገፉ ከብዙ አቅጣጫ ከጠላት የሚመጡ ፈተናዎችን ለማለፍ ባደረጋቸው መፍጨርጨር ዉስጥ የተፈጠረውን የተቋም ረሀብ ለማስታገስ ከመሰረታቸው ተቁማት መካከል ማህበራችን የአማራ ተማሪዎች ማህበር /አተማ/ አንዱ ነው፡፡ በመሆኑም የአማራ ተማሪዎች ማህበር /አተማ/ ከተመሰረተበት ከ ነሀሴ 28/2010 ዓ.ም ጀምሮ ላለፉት ዓመታት የሰራቸው ስራዎች እጅግ በርካታ ቢሆኑም በጥቂቱ ለመዳሰስ ያህል፡- 1) በ 2013 ዓም የነበረውን የክተት ጥሪ ተከትለው የዘመቱ ና የተሰው የፋኖ ፤ የሚሊሻ ፤የልዩ ሀይልና ጠመከላከያ አባላትን ቤተሰብ ትኩረት አድርጎ በነደፈው ፕሮጀክት 4000 የዘማች ቤተሰቦችን አካቶ ለእያንዳንዳቸው የ4000 ድጋፍ አድርጉል፡፡ 2) በጦርነት ወቅት ወላጆቻቸውን ያጡ እንዲሁም ረዳት አልባ የሆኑ ሕፃናትን ለማግዝ በቀረጸው ፕሮጀክት መሰረት 380 ህጻናትን አቅፎ 18 ዓመት እስኪሞላቸው ድረስ እንደወላጅ የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ እያሟላ እያሰተማረ ይገኛል ፡፡ 3) የትግራይ ወራሪ ሀይል ሀገሪቱ ላይ ያወጀውን ጦርነት ተከትሎ ከተከሰቱ ሁናቴዎች መካከል የማህበራዊ አለመረጋጋት ችግር አንዱ ነበር፡፡ከዚህ ጋር ተያይዞ በጦርነቱ ወቅት በቀጥታ የተጎዱ አካባቢዎች ላይ የነበሩ የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ተፈታኞች ላይ የነበረው ጫና ቀላል ስላልነበረ በተረጋጋ መንፈስ መፈተን ስላልቻሉ የውጤት መበላሸት አጋጥሞ ነበር፡፡ ነገር ግን የትምህርት ሚኒስቴር በዲጋሚ እንዲፈተኑ እድል መስጠቱን ተከትሎ የአማራ ተማሪዎች ማህበር /አተማ/ መምህራንን በማሰባሰብ ና ወጪያቸውን በመሸፈን በ6 የአማራ ክልል ዞኖች እንዲሁም በአፋር ክልል የድጎማ ትምህርት እንዲሰጥ አድርጓል፡፡ ማህበራችን የአማራ ተማሪዎች ማህበር (አተማ) እነዚህንና መሰል ተግባራትን ሲያከናውን ሁኔታዎቹ አልጋ ባልጋ ሆነውለት ሳይሆን ይልቁኑ ከተመሰረተበት ዋነኛ አላማ አንፃር የአማራ ተማሪዎችን መብት ለማስከበር ከደምቢ ዶሎ ዩኒቨርስቲ የአማራ ተማሪዎች መታገት እስከ ትላንት የመቅደላ አምባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች መታገድ ድረስ እልህ አስጨራሽ ትግል እያደረገ አሁን ባለበት ደረጃ ደርሷል። ይሁንና የአማራ ህዝብ በየጊዜው ከሚያነሳቸው የህልውና ጥያቄዎች ጋር ተያይዞ በርካታ ማህበራትና የፓለቲካ ድርጅቶች ቢመሰረቱም ተቋማዊ ችግርን የመቋቋም አቅማቸው ከጠላት በኩል የሚመጣን ተቋም አፍራሽ ውጫዊ እና ውስጣዊ ፈተናዎችን ተቋቁመው የተመሰረተበትን ዓላማ አንግቦ መሻገር ሲሳናቸው ይስታዋላል። እናም ማህበራችን የአማራ ተማሪዎች ማህበር (አተማ) እንደ አንድ የአማራ ተቋም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከላይ የዘረዘርናቸው የአማራ ተቋማት ሁሉ የገጠማቸው ተቋማዊ ፈተናዎች እየፈተኑት ይገኛል። አሁን ላይ ማህበሩ የገጠመው ችግሮች በአንድ ለሊት የተፈጠሩ ሳይሆን ይልቁንም ረዘም ላሉ ጊዜአት ከፊል ገፅታቸው ሲታይ ቆይቶ አሁን ግዝፈት ነስተው የተገለጡ ናቸው። በማህበሩ ውስጥ በተለይም ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ውስጥ በየጊዜው የነበሩ መኮራረፎች ለጊዜው በማንኛውም ተቋምና ስራ ውስጥ የሚያጋጥሙ መደበኛ ክስተቶች ቢመስሉም ውለው ሲያድሩ ግን ጤናማ ያልሆኑ ፍላጎቶች የወለዷቸው መሆናቸው አልቀረም ። እነዚህ ጤናማ ያልሆኑ ፍላጎቶች በበኩላቸው በማህበሩ ዓላማና የእለት ከእለት እንቅስቃሴ ላይ በየጊዜው እንቅፋቶችን የሚያስቀምጥ ጤናማ ያልሆነ ቡድንን ፈጠሩ። የዚህ ቡድን አባላት ልዩ ምልክታቸው በማህበሩ ውስጥ በነበራቸው ቆይታ እዚህ ግባ የሚባል ተግባር ያላከናወኑ ይልቁንም የሚሰሩትን እየተከታተሉ መተቸትና ማውገዝን ዋነኛ ተግባራቸው አድርገው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ መሆናቸው ነው። መነሻ ሀሳባቸው በማህበሩ ውስጥ የሚታዩ ችግሮች ይፈቱ የሚል ቢሆንም ግባቸው ግን ችግሮቹ እንዲፈቱና ማህበሩ የተመሰረተበትን ዓላማ ማሳካት የሚችልበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ ከመስራት ይልቅ በነዚህ ጥያቄዎች ሽፋን የራሳቸውን ግላዊና ቡድናዊ ፍላጎቶች ለማስፈፀም የሚደክሙ መሆናቸው ሌላው መገለጫቸው ነው። በማህበሩ ውስጥ ችግሮች መኖራቸውንና መፈታት ያለባቸው እንዲሁም ተጠያቂነት የሚያስከትሉ ከሆነ ተጠያቂ መሆን ያለበት አካል መኖር እንዳለበት የማይካድ ቢሆንም እነዚህ አካላት ግን የተቋሙ ችግር አሳስቧቸው በቅንነት የሚሰሩ ሳይሆን ፍላጎታቸውን ለማስፈፀም ስንጥቅ የሚፈልጉ ናቸው። ይህ ስብስብ ተቋምን ከግለሰብ መለየት በተሳናቸውና በግለሰባዊ ጥላቻ በሰከሩ ሰዎች የታጨቀ ነው። ቡድኑ በዋናነት በማህበሩ ም/ሊቀመንበር በነበረው ኪሩቤል ጎቤ፣ ሂሳብ ሹም በነበረው ሰምረአብ አየለ፣ አደረጃጀት ዘርፍ ሀላፊ በነበረው ኤርሚያስ ጥጋቤ፣ ም/አፈጉባኤ በነበረው ዮናስ ገብሬ እና ተመሳሳይና ተቀራራቢ ፍላጎት ባላቸው የቅርንጫፍ ጽ/ቤት ሰብሳቢ በነበሩ ግለሰቦች አብርሀም ብርሀን የባህርዳር ቅርንጫፍ ሰብሳቢ የነበረውን ጨምሮ የሚመራ ሲሆን የዚህ አፍራሽና አፈንጋጭ ቡድን ዋና አስተባባሪዎች ተቋሙ ላይ በነበራቸው የሀላፊነት ጊዜያት ያላቸውን የተቋም ደንታቢስነት እና ተቋም የማፍረስ ተግባር ማሳያ ይሆን ዘንድ ከዚህ በታች ስለ ልጆቹ ለመግለፅ ያክል ። በዚህ ሰአት በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች አማራ የሆነ ፍጡር በሙሉ በሁለንተናዊ ችግር ውስጥ ባለበት ሁኔታ እነሱ ግን ራሳቸው ትክክለኛ ታጋይና የማህበሩ ጠበቃ አድርጎ በማሰብ በተግባር ግን ከአገዛዙ በኩል በሚታደላቸው ገንዘብ ተቋሙን በመቀየር አዳርና ውሏቸውን ከመንግስት ፀጥታ አካላት ጋር በማድረግ የቀድሞ የማህበሩን ሊቀመንበር እና ፣አፈጉባኤ ጨምሮ አንድም ቀጥታ ጠቋሚ በመሆን ሌላ ጊዜ የውሸት ውንጀላ ፈጥሮ በመክሰስ ወንድሞቻቸውን እንዲታፈኑና እንዲታሰሩ ሲያደርጉ ቆይተዋል። ከዚህም በተጨማሪም ከኢትዮጵያ ሲቪክ ማህበራት ኤጀንሲ ጋር ኢ-መደበኛ ግንኙነት በመፍጠር የማህበሩ ህጋዊ ማህተም ባለበት ሌላ ተጨማሪ ማህተም በማስቀረፅ የማህበሩ ሂሳብ ሹም የነበረውን ግለሰብ በመጠቀምና የሊቀመንበሩን ፊርማ በማስመሰል በህገወጥ መልኩ ገንዘብ የሚመዘብሩ ፣በየቅርንጫፍ ጽ/ቤት እንዲሁም በአባላት መካከል አላስፈላጊ መጠራጠርና መከፋፈልን የሚነዙ እንዲሁም የጎጠኝነት ትርክት የሚያሰርፁ እና የሚያራምዱ ናቸው። በዋናነት ግን ማህበሩ ቤት ዘግቶ ያከናወናቸውን ለተቋሙ መሰረት ሊሆኑ የሚችሉ ተቋማዊ ሚስጥሮችን ማለትም የተለያዩ ሰነዶችና ስትራቴጅዎችን ለጠላት አሳልፎ በመሸጥ ፍፁም ባንዳነታቸውን በገሀድ ገልጠዋል። የዚህ አፍራሽ እና አፈንጋጭ ቡድን ማህበሩን ለማዳን በሚል ከሚያነሷቸው የሽፋን ጥያቄዎች መካከል የፋይናንስ ግልፀኝነት ችግርና የውጭ ግንኙነትን በተመለከተ ሲታይ የነበረው የመርህ ጥሰት ጎንደር ላይ በነበረው የስራ አስፈፃሚ ውይይት እና ስምምነት መሰረት ጥቅምት 15/2015 ዓ.ም ወልዲያ ከተማ በተደረገው የማህበሩ አመታዊ መደበኛ ጠቅላላ ጉባየ በቀረበው የኦዲት ሪፖርት እና በእለቱ ቀርቦ በፀደቀው የውጭ ግንኙነት መርህና የኮሚንኬሽን ስትራቴጅ ለመፍታት የተደረገውን ፍፁም ልዩነት የሌለበትን ጥረት ወደ ጎን በመተው ከጉባየው መልስም ችግሮች እንደተባባሱ አድርጎ ሲያቀርቡ ተስተውሏል።እናም በዚሁ መደበኛ ጠቅላላ ጉባየ የቅርንጫፍ ጽ/ቤቶችን ማጠናከርና ተሀድሶ ማድረግ እንዲሁም ለማዕከላዊ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ እጩ የሚሆኑ ተማሪዎችን መለየት ከዚያም አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባየ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑ በጉባየው ተወስኖ ነበር። ይሁን እንጅ በየቅርጫፍ ጽ/ቤቶች ግልፅና ተቋምን ሊገነባ የሚችል ተሀድሶ(reform) ከማድረግ ይልቅ በስውር ከማደራጀት እንዲሁም አላማውን ለማስፈፀም ድብቅ ተልዕኮ ከመስጠት ባሻገር ሌሎች በመደበኛ ጉባየው የተወሰኑ ቅድመ ሁኔታዎች ባልተሟሉበት ሁኔታ ህዳር 25/2015 ዓ.ም በማህበሩ መተዳደሪያ ደንብ በተቀመጠው መሰረት ስልጣን ባለው አካል ያልተጠራ ተቀባይነት የሌለው ጠቅላላ ጉባየ በመጥራት በወቅቱ የጠቅላላ ጉባኤው አባላት ያልሆኑና አንዳንዶቹ የየትኛው ቅርንጫፍ ተወካዮች እንደሆኑ በውል የማይታወቁ እንዲሁም በማህበሩ ሕጋዊ የእውቅና ሹመት ደብዳቤ ያልተሰጣቸው አካላትን በመሰብሰብ፤ ከሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ውስጥ ሊቀ መንበሩ፣ የጽ/ቤት ኃላፊው እና የሕ/ግንኙነት ኃላፊው ባልተገኙበት ሁኔታ አንዳንዶቹን የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በማታለል ጉባኤው ላይ እንዲገኙ በማድረግ ‹‹ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴና ሌሎች አመራሮችን አስመርጫለሁ›› በማለት የጉባኤው አባላት ላልሆኑ አካላት ጭምር የሹመት እደላ አከናውኗል፡፡ ከዚህ በኋላ ቡድኑ ማህበሩን ለመረከብ እንቅስቃሴ ከማድረጉ በተጨማሪ ‹‹የአማራ ትውልድ ተቋም›› የተሠኘ የቴሌግራም ግሩፕ በመክፈት ሐሰተኛና የጥላቻ መረጃዎችን ማሰራጨት የጀመረ ሲሆን ምናልባትም ችግሩን በንግግር ለመፍታት በመሥራችና የቀድሞ የማህበሩ ሥራ አስፈጻሚዎች አማካኝነት ታኅሣሥ 09/2015 ዓ.ም በባሕር ዳር ንግግር ቢደረግም አፈንጋጭ ቡድኑ ካለው ግትር ፍላጎት አንጻር መግባባት አልተቻለም፡፡ ነገር ግን ጥረቱን በመቀጠል ጎንደር ከተማ ተጨማሪ ውይይት ተደርጎ በጊዜያዊነት መደበኛ ሥራዎችን አቁመን መፍትሔው ላይ ብቻ ትኩረት እንድናደርግ ከሽማግሌዎች በቀረበው ሐሳብ ተስማምተን የነበረ ቢሆንም ቡድኑ ግን ብዙ ጊዜ ውስጥ ለውስጥ ሌላ ጊዜ በግልጽ እየተንቀሳቀሰ ቅርንጫፎች ላይ የጥላቻ ስብከት ከመስበክ ባሻገር ከገዥው የብልፅግና መንግስት ጋር ጥብቅ የሆነ ግንኙት በመፍጠ የተቋሙን አመራሮች ማሳደድ እና ማሳፈኑን ገፍቶበታል ። እናም የቡድኑ ዋነኛ ድጋፍ ሰጪ ብልጽግና መንግስት በመሆኑ ማህበሩን የማዳኑ ጉዳይ ከሥርዓቱ እጅ ፈልቅቆ የማውጣት ተግባር መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል፡፡ በእኛ በኩል እስካሁን ድረስ ስለጉዳዩ ይፋዊ መግለጫ ከመስጠት የተቆጠብነው በሁለት ምክንያቶች ነው፡፡ እነርሱም፡- የመጀመሪያው አፈንግጠው የወጡት አባላት ምናልባትም ወደ ቀልባቸው ይመለሳሉ፤ በውይይትም ይፈታል በሚል ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በአገዛዙ ምክንያት በመከራ ውስጥ ለሚኖረው የአማራ ሕዝብ ከችግሩ መውጣት የሚያስችል አንዳች ቁም ነገር በመሥራት ፋንታ ተጨማሪ የቤት ሥራና ተጨማሪ ሐዘን የሚያመጣ መግለጫ መስጠት ተገቢ አይደለም በሚል እሳቤ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በማህበሩ ስም በጥቅም የተደራጀው ቡድን ይህን እንደመልካም አጋጣሚ በመጠቀም ራሱን ሕጋዊ አድርጎ ለማቅረብና ከጀርባ ካሉት በርካታ ተቋማት፣ ቡድኖችና ግለሰቦች ጋር በመተባባር ማህበሩን ለማፍረስ ካልሆነም ለራሱ ጥቅም ማስፈጸሚያ ለማድረግ በከፍተኛ ሁኔታ እየተንቃሰቀሰ በመሆኑ እውነታውን ለሕዝብ ይፋ ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ ይህንን መግለጫ አውጥተናል፡፡ በቀን 28/05/2015 በተደረገው ህጋዊ ጠቅላላ ጉባየ ባደለግን ማግስት ባወጣነው መግለጫ ላይ ይፋ ባረግነው መሰረት 1ኛ ሲሳይ መልካሙ-የማህበሩ ሊቀመንበር 2ኛ በለጠ አቤ- የማህበሩ ም/ሊቀመንበር 3ኛ አለባቸው ያስር- የማህበሩ የጽ/ቤት ኃላፊ 4ኛ በላይሁን ኃ/ማርያም-የማህበሩ ሒሳብ ሹም 5ኛ አብ አግማስ- የማህበሩ የሕ/ግንኙነት ኃላፊ 6ኛ አብርሃም ፈንታ- የማህበሩ የሕግ ጉዳዮች ኃላፊ 7ኛ እዘዝ ሞላ- የማህበሩ የጥናትና ምርምር ዘርፍ ኃላፊ 8 መታደል ጓዴ- የማህበሩ የሴቶች ጉዳይ ኃላፊ 9ኛ ኤፍሬም ጎበዜ-የማህበሩ የአባላት ጉዳይ ሃላፊ 10. የአብሥራ ደስታ- የማህበሩ የጠቅላላ ጉባኤ ሰብሳቢ 11.መለሰ ባበይ- የማህበሩ ም/ጠቅላላ ጉባኤ ሰብሳቢ 12.ሀብታሙ አንለይ- የጠ/ጉባኤ ጸሐፊ 13.አባትነህ ለወዬ- የኦዲትና ቁጥጥር ሰብሳቢ 14.ይኼነው ታደሰ- የኦዲትና ቁጥጥር ም/ሰብሳቢ 15.አርጋው ታደለ-የኦዲትና ቁጥጥር ጸሐፊ 16.ታደለ ስመኝ- የኦዲትና ቁጥጥር አባል 17.ዮናስ ተሾመ- የኦዲትና ቁጥጥር አባል ሆነው መመረጣቸው የሚታወስ ነው። በመሆኑም ይህ የተመረጠ አዲስ ስራ አስፈጻሚ የአማራን ሕዝብ የተቋም ረሃብ በልኩ የተረዳ በመሆኑ ከአገዛዙ በኩል የሚመጣ ብዙ የአማራ ተቋማትን ፈትኖ የጣለ ተቋማዊ ፈተናን የተረዳ በመሆኑ የአማራ ተማሪዎች ማህበር /አተማ/ የዚህ ገፈት ቀማሽና ሰለባ እንዲሆን የማይፈቅድ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የአማራ ተማሪዎች ማህበር /አተማ/ ፡- 1) ከዚህ በኋላ አገዛዙም ይሁን ማንም አካል ጉልበት በተሰማው ቁጥር የሚያፈርሰው የአማራ ተቋም እንዳይኖር የአማራ ተማሪዎች ማህበር/አተማ/ አበክሮ ይሰራል፡፡ 2) በቀጣይ በተቋማት ዉስጥ የተሰገሰጉ ሆድ አደሮች በያሉበት ተቋም ውስጥ ነገ ላይ ተቋማቸዉን የማፍረስ ድብቅ ተልዕኮ እንዳያስፈጽሙ አተማ በራሱ ላይ የተነሱበትን የውስጥ ጠላቶች ህጋዊ እርምጃ በመውሰድ አስተማሪ ሆኖ ይቀጥላል፡ 3) አዲስ ለሚወለዱና ለሚንገዳገዱ የአማራ ተቋማት አተማ በሚወስደው እርምጃ አርአያ ሆኖ ይቀጥላል፡፡ 4) ስርዐቱ የማህበረሰቡን ምልክቶች በማሰርና በማንገላታት ምልክት አልባ እያደረገ ስለሆነ በሚታሰሩ እንደነ አርበኛ ዘመነ ካሴ ባሉ ሰዎች ዉስጥ የማህበረሰቡን ስነልቦና እየጎዳ ስለሆነ አተማ ደግሞ የማህበረሰቡ እሴትና ስነልቦና እንዲሁም ምልክት በሰላማዊ መንገድ ማስጥበቅ ግደታው ስለሆነ ይህን ለማስጠበቅ እንቅስቃሴ የሚጀምር መሆኑን ፡፡ 5) ስርዐቱ የአማራን ህዝብ ስደት፤ሞትና መፈናቀል እንዲሁም የነቁ አመራርና አባላትን ማሰርና ማዋከቡን እንዲያቆም ጥሪ ማድረግ፤ ካላቆመ ግን በራሳችንና በሕዝባችን ትግል ለማስቆም እንቅስቃሴ የምንጀምር መሆኑን ስንገልጽ ከላይ የዘረዘርናቸውን ቀጣይ የትግል እንቅስቃሴዎችን እዉን ለማድረግ በሀገር ዉስጥና በዉጭ ሀገር ያላችሁ የአማራ ሲቪክ ማህበራት፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ፤የሚዲያ ተቋማት ፤የማህበራችን አባላትና ደጋፊዎች እንዲሁም መላው የአማራ ሕዝብ ከጎናችን እንዲሆን ስንል ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ፡፡ አተማ፡የአማራ ትውልድ ተቋም!!! የካቲት ፳፪/፳፻፲፭ ዓ.ም “ውድ የአሻራ ሚዲያ ቤተሰቦች የአሻራ ሚዲያ ቻናልን ላይክና ሰብስክራይብ በማድረግ ድጋፋችሁን ታሳዩን ዘንድ በአክብሮት እንጠይቃለን።” ለፈጣንና አዳዲስ መረጃዎች አሻራ ሚዲያ የአይበገሬዎቹ ልሳን:- // Youtube:- https://www.youtube.com/channel/UCPmgFzP2ZPmdGjHxXjigJaw // Facebook:- https://www.facebook.com/asharamedia24 // ቴሌግራም:- https://t.me/asharamedia24
Source: Link to the Post