ከደብረዘይቱ (ቢሾፍቱ) ኢሬቻ እስከ ወልድያው ጥምቀት በዓል የዘለቀውና ዛሬ ደግሞ ወደ ለየለት የዘር ማጥፋት (Genocide) የተሸጋገረው የትግራይ ፋሽስቶች ፍጅት
በዶክተር አሰፋ ነጋሽ – (ሆላንድ ሀገር ነዋሪ የሆነ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ)
Email address: [email protected]
ክፍል አንድ (፩) –
ይህንን ጽሁፍ የጻፍኩት በሰሜን ወሎ ዋና ከተማ በወልዲያ የቃና ዘገሊላ በዓል በተከበረበት ወቅት የፋሽስቱ የወያኔ ትግሬዎች መንግስት የፈጸመውንና በሌሎችም የኢትዮጵያ ክፍሎች እየፈጸመ ያለውን ፍጅትና ህዝብ የማፈናቀል ድርጊት የተሰማኝን ለአንባቢዎች ለማካፈል ነው። የወልዲያን ፍጅት ተከትሎ ወራሪው የትግሬ ፋሽስታዊ መንግስት በሰሜን ወሎ ህዝብ ላይ የከፈተው በእኔ እይታ የዘር ማጥፋት (genocidal war directed against the people of northern Wello by the Tigrean fascist army) ሲሆን በደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ በሚኖሩት ወገኖቻችን የሆኑ የኦሮሞ ተወላጆችም ላይ የከፈተው የፍጅትና የማፈናቀል ድርጊት በአንድ ፋሽስት መንግስት የሚካሄድ የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው።
የጥምቀት በዓል በኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ዘንድ እጅግ ታላቅ መንፈሳዊ በዓል ነው። በዚህ በዓል ላይ የወልድያ ወጣቶች ታቦት አጅበው፤ የቀድሞዎን የኢትዮጵያ ባንዲራ ይዘው እየዘፈኑና እየጨፈሩ ኮከብ የሌለበትን የቀድሞ የኢትዮጵያ ሰንደቅዓላማ ይዘው ይሄዱ ነበር። ለወያኔ ሥርዓት ያላቸውንም ተቃውሞ ሰላማዊ በሆነ መንገድ በመናገር ይገልጹ ነበር። በዚህ ወቅት ትንኮሳ (ህዝብን ተንኩሶ ጠብ በማስነሳትና በዚህም ሳቢያ መልሶ ህዝብን ጥፋተኛ አድርጎ መኮነንና መፍጀት ፋሽስቶች ከሚታወቁባቸው ዓይነተኛ ባህርያት አንዱ ነው። ይህ የወያኔ ድርጊት የጀርመን ናዚዎች እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ1933 ዓ.ም. የጀርመንን ፓርላማ አቃጥለው ኋላ ላይ የጀርመን ኮሚኒስቶችን ለድርጊቱ ተጠያቂ አድርጎ በመወንጀል ኮሚኒስቶችን ሰብስበው ያሰሩበትንና የፈጁበትን ድርጊት ያስታውሰኛል) በመፈጸም ጠብ ማንሳት ባህርያቸው የሆኑት በትግሬ ወታደሮች የተደራጀው የአጋዚ ጦር ወጣቶቹ የያዙትን የኢትዮጵያ ሰንደቅዓላማ ለመቀማት ሞከሩ። የቀድሞውን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ለመንጠቅ የአጋዚ የትግሬ ወታደሮች ባደረጉት ትንኮሳና በጀመሩት በዚህ ግጭት አሳበው ተኩስ በመክፈት አስራ ሁሉት ሰዎችን መግደላቸውንና አስራ አምስት ሰዎችን ማቁሰላቸው ታውቋል (ቁጥሩ ከዚህ በእጅጉ ሊበዛ ይችላል)። ሌላው አስገራሚው ነገር በዚህ ህዝቡ ታቦት ተሸክመው በሚሄዱት ሰዎች መካከል ቀደም ብሎ በተጠና መልክ የመለስ ዜናዊን ፎቶግራፍ የያዙ የህወሃት ሰዎች ህዝቡ መካከል በመግባት ህዝቡን ሆን ብለው ለመተንኮስ ሞክረዋል። ታቦት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ እጅግ የተከበረ የኃይማኖታቸው አንድ መገለጫ መሆኑ ቢታወቅም በይሉኝታ-ቢስነታቸው በሚታወቁት የትላንትናዎቹ የትግራይ ጦረኞችም ሆነ የዛሬዎች የወያኔ ትግራይ ተጋዳላዮች ዘንድ ታቦት አክብሮት የሚቸረው ነገር አይደለም። በጦርነትም ውስጥ እንኳን የሃይማኖት ተቋማት ሆን ተብለው የጥይትና የቦምብ ዒላማ አይደረጉም። ታቦት ተሸክመው የሚጓዙ ቀሳውስት ላይም አስለቃሽ ጢስ የሚተፋ ጥይት አይተኮስም።በኢትዮጵያ ታሪክ የቅርብ ዘመን ታሪክ ውስጥ ቤተክርስቲያኖችና ታቦታት የጦርነት ሰለባ የሆኑት በጣሊያን የፋሽስት አገዛዝ ዘመን (1928-1933 ዓ.ም.) እና በዛሬው የወያዎች የፋሽስት አገዛዝ ዘመን ነው። ሃይማኖታዊ ተቋማትን ማክበር በትግራይ ጦረኞች ዘንድ ጥንትም ሆነ ዛሬ የሚታወቅ ነገር አይደለም። የታሪክ ገጾችን ስናገላብጥ የትግሬ መሪዎችም ሆነ ወታደሮች ብዙ የክርስቲያን ደብሮች ካሉባት ትግራይ የወጡ መሆናቸውን እንረዳለን። ይሁን እንጂ የዛሬዎቹ የትግራይ ፋሽስቶችም ሆኑ ከመቶ ሰላሳ ዓመታት በፊት የነበሩት ክርስቲያኖቹ የትግራይ ወታደሮችም ሆኑ መሪዎቻቸው በጥቅማችውና በሥልጣናቸው ላይ ሲመጣ ለታቦትም ሆነ ለተከበሩና የቅድስና ማዕከላት ተደርገው ለሚታዩ ኃይማኖታዊ ተቋማት (ቤተክርስቲያን፤ ገዳሞች ወዘተ) እና አገልጋዮቻቸው (ፓፓሳት፤ ቀስውሳት፤ ዲያቆናት) ወዘተ አክብሮት የሌላቸው አረመኔዎች እንደ ሆኑ በተደጋጋሚ አስመስክረዋል። ይህንንም ድርጊታችውን አንድ ነቃሽ የታሪክ ዋቢ እየጠቀስኩ በሚከተለው መልክ አስረዳለሁኝ። እነሆ ከዚህ በታች ለአንባቢ ግንዛቤ እንዲረዳ በጥቅስ ውስጥ ያሰፈርክት ድርጊት የተፈጸመው በኢትዮያ አቆጣጠር በ1880 ዓ. ም ዐጼ ዮሃንስ የሚባለው ከትግራይ ወጥቶ የነገሰ የኢትዮጵያ መሪ ኢትዮጵያን ባስተዳደረበት ዘመን ነው። ዐጼ ዮሃንስ የጎጃሙ ንጉሥ ተክለኃይማኖትና የሸዋው ንጉሥ ምንሊክ አድመው ግንባር በመፍጠር ሥልጣኔን ሊገዳደሩ(ሊፈታተኑት) ነው በሚል ፍራቻ በምጽዋ ላይ ሰፍሮ ያለውን የጠላት ኃይል (የጣሊያንን ጦር) ወግቶ ከኢትዮጵያ ግዛት በማስወጣት ፈንታ ጦሩን ይዞ ወደ ፊቱን ወደ ጎጃም አዞረ። በፍጥነት ወደ ጎጃም በመመለስ የጎጃሙ ንጉሥ ተክለሃይማኖት ከንጉሥ ምንሊክ ጋር አድሞብኛል በሚል ቁጣና ንዴት ንጉሥ ተክለኃይማኖትን እቀጣለሁኝ ብሎ ተነሳ። በዚህም ምክንያት ዮሃንስ ጦሩን በጎጃም ህዝብ ላይ አሰማርቶ የጎጃምን ህዝብ ለስድስት ወራት ያህል ሲዘርፍና ሲያዘርፍ ቆየ።
ጣሊያኖችን እዚያ ምጽዋ ላይ ትቶ በመምጣቱም ምክንያት ነው ጣሊያኖች ከምጽዋ ገፍተው ባህረ ነጋሽ ይባል የነበረውን የኢትዮጵያን ክፍለ ሀገር ኋላ ላይ ኤርትራ የሚል የቅኝ ገዢዎች ስም በመስጠት ከኢትዮጵያ ቆርጠው በቅኝ ገዢነት ሊያስተዳድሩ የበቁት። ይህ የዐጼ ዮሃንስ ስህተት በኋላ ላይ ምንሊክ ላይ ተላኮ ምንሊክ ለኤርትራ መገንጠል ምክንያት ሆነ እየተባለ በትግራይና በኤርትራ ተወላጆች ተከሰሰ። እስቲ ዮሃንስና እሱ ይመራው የነበረው ከትግሬ የተነሳ ጦሩ ለስድስት ወር ጉጃምን ሲያጠፋ እንዴት አድርጎ ቤተክርስቲያኖቻችን እንዳፈረሰና ታቦታትን እንዳረከሰ ከሚቀጥለው የዓለቃ ተክለ ኢየሱስ ዋቅጅራ ሐተታ እንናንብብ። ከልጅነታቸው ጀምሮ ጥርስ እየሰበሩ በሚያድጉበት ልክ የለሽ የአማራ ጥላቻና በዘረኛነት ልክፍት አይናቸው የታወረው የትግራይ ተወላጆች ማናቸውም አማራ የሚባል ሰው የጻፈው ነገርም ሆነ ታሪክ የፈጠራ ድርሰት ስለሚመስላቸው ይህ ከዚህ በታች የጠቀስኩት ጽሁፍ ምንጭ የሆኑት ጸሀፊ የኦሮሞ ተወላጅ መሆናችውን አስቀድሜ መግለጽ እወዳለሁኝ። የእኚህ ጸሃፊ የሆኑት ሰው ሥም አለቃ ተክለኢየሱስ ዋቅጅራ ሲሆን የመጀመሪያ ስማቸው ነገሮ ይባል ነበር። ነገሮ ዋቅጅራ ራስ አዳል (ኋላ ንጉሥ ተክለሃይማኖት የተባሉት የጎጃም ንጉሥ) የዛሬው ምሥራቅ ወለጋን ለማቅናት ወደዚያ በሄዱበት ጊዜ ማርከው ከወለጋ ወደ ጉጃም ካመጡአቸው ስምንት የኦሮሞ ልጆች አንዱ ነበሩ። እዚያው ጎጃም አድገው፤ ተምረውና ኖረው የሞቱ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሠዓሊ እነደነበሩ ለመግለጽ እፈልጋለሁኝ። እኚህ ታላቅ ሰዓሊ በንጉሥ ተክለ ሃይማኖት ፈቃድ ቀደም ሲል የንጉሱ ልጅ የነበሩት ራስ በዛብህ የተባሉት ሰው ሚስት የነበረችውን ወ/ሮ ዓለሚቱ መርሻን ማግባታቸው ተገልጿል። እዚህ ሁሉ የነገድ ግንድ ቆጠራ ውስጥ የገባሁት ወድጄ እንዳልሆነና ይህንን ከዚህ በታች በስፋት የጠቀስኩትን ጽሁፍ ዛሬ የወያኔ ትግሬዎች በጠላትነት የሚያዩት፤ “ተንኮለኛውና የትግሬ ደመኛ ታሪካዊ ጠላት የሆነው አማራ” እንዳልጻፈው ለማስረዳት ያህል ነው። አለቃ ተክለ ኢየሱስ ዋቅጅራ የተዉልን የታሪክ ማስታወሻ እነሆ እንደሚከተለው ቀርቧል።
“የንጉሥ ምንሊክንና የንጉሥ ተክለሃይማኖትን ክዳት ዐጼ ዮሃንስ ባወቀ ጊዜ ተናደደ። በዚያም በምጽዋ በኩል ከኢጣሊያኖች ጋራ ተሰላልፎ ነበረና ጠባቂ ጦር ከፍሎ ትቶ በ1880 ዓመተ ምህረት በነሐሴ መጥቶ ጎጃምን ዘረፈ። ንጉሥ ተከለ ሃይማኖትም ስንቁን አስልቶ እቃውን አሰናድቶ በጅበላና በሙተራ አምባ ገባ። አቡነ ሉቃስ ግን አምባ አልገባም። ብቻ ለማስታረቅ ሲጥር ከዐጼ ዮሃንስ ጋራ ጉሊት ከረመ። ዐጼ ዮሃንስም ጎዛምን ላይ ሰፍሮ አምባውን ሊሰብር በጭምትና በማይ አፋፍ መድፍ ጠመደ። ግን አልሆነለትም። ኃይለኛውም መድፍ ጅበላን እያለፈ ከዓባይ በረሃ ወደቀ። ቀላሉም መድፍ የአምባውን ገደል እየመታ ቀረ።
ያን ጊዜ የንጉሥ ተክለ ኃይማኖት የመድፍ ዘበኛ አለቃ ባሻ አስናቀ የሚባል ነበረ። ጅበላ ላይ ሆኖ ጭምት ላይ ከተጠመደው መድፍ ተመልክቶ ቢተኩስ የመድፉ ዓረር በመድፍ አፍ ገብቶ ከመንኮራኩሩ ገልብጦ ተኳሹን ጨምሮ ገደለ። ባላምባራስ ጊዮርጊስ የሚባል ጀግና የግሪክ ሰው ነበረ። እርሱም ደግሞ ብዙ ትግሬ ገደለ። ከዚህ በኋላ ዐጼ ዮሃንስ ጭምት አፋፍ መቀመጡን ተወ። ከዚህ በኋላ በጎዛምንና በማቻክል የተገኘውን የቤተክርስቲያን ሳንቃ እየነቀለ እያመጣ በጭምት አፋፍ የአረር ማብረጃ ተራውን አቁሞ ማገረው። እየፈለጠ አነደደው። ታቦቱንም ከመንበሩ እየበረቀሰ በየሜዳ ጣለው። የዚህ ጊዜ አቡነ ሉቃስ ዐጼ ዮሃንስን ተቆጣ። ደርቡሽን አጠፋለሁ ብየ መጣሁ ያልኸው ለጉጃም ደርቡሽ አንተ ሆንኸው አለው። ደግሞ አምባውን ሰብሮ ሌሊት ገባ በጨረቃ ጭፍራ ሰደደ። ከአምባው ጥግ ሆነው በስተጎድን መውጫ ሲፈልጉ ማለዳ እንጨት ለቃሚ አያቸውና ተናገረ። የዚህ ጊዜ በናዳ ተለቀቀው። ዘበኞችም እያባረሩ በውትርን ጨረቻ ብዙ ትግሬ ገደሉ። ያን ጊዜ ዐጼ ዮሃንስ ከዓባይ እስከ ዓባይ ጭፍራ ሰዶ ጉጃምን አዘረፈ። ዝርዝሩን እህል እያጨደ ለርኩስ አበላው። እላሙንና በሬውን አንገቱን ሳይባርክ ነቀላውንና ጭኑን፤ ሽንጡን እየነቀለ፤ እየቆረጠ በላው። ሲናድሩን አቋምጦ ይዞ በቆላውም በደጋውም ጠል ጠል ሲል በትግሬ ቋንቋ ዋይለይ፤ ትፍለስ ክነኃት (እንዲህ ካደረግህ አጠፋሃለሁ፤ እደመስስሃልሁ የሚል ትርጉም አለው) እያለ እያስፈራራ ልብስ ሲገፍ የንጉሥ ተክለሃይማኖት አሽከሮች ጀግኖች አምባ ያልገቡት እነደጃች ወዳጆ ነበሩ። መርጡ ለማርያምን ታደጉ። ብዙ ትግሬ ገደሉ። በስናድር በጥይት ሻሩ። ደገኛ በአምጃው፤ ቆለኛ በክትክታው እየተደበቀ ትግሬን የአሞራ ቀለብ አደረገው። ስናድሩንና ጥይቱን ሞሸለቀው። ያን ጊዜ ደጃች ማሩ የሚባል ትግሬ ዲማ ጊዮርጊስ ደረሰ። ዋሻውን ሊሰብር ዕቃ ቤቱን ሊበረብር ወረራ አደረገ። ዲሞችም የቤተክርስቲያኑን ውድም በሶስት በር ሁሉ ሳንቃውን በድንጋይ ረብርበው ዘግተው ተቀምጠው ነበር። የገጠሩም ዕቃ ብዙ ገብቶ ነበረ። መግቢያ ባጣ ጊዜ በሳንቃው ቀዳዳ አስገብቶ ተኮሶ አንድ ሰው ገደለ። የዚህ ጊዜ ዲሞች መልክአ ጊዮርጊስ ሰባት ጊዜ ደግመው ረገሙት። ወዲያው ያንን የተኮሰውን ትግሬ ቁርጠት ተለቀቀው። ላብ አላበው። ጓደኞቹ አዝለው ከገበያው አጠገብ ከሰፈር ወስደው ከድንኳኑ አግብተው አስተኙት። ህማሙ በበረታበት ጊዜ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተሳለ። ሲናድሩንና የወገቡን ጥይት ሰጥቶ ከጸበሉ ጠጥቶ ዳነ። ከዚህ በኋላ ደጃት ማሩ ደነገጠ። ገዳዩ ታቦትዬ እያለ ተደነቀ። ዋሻውን አይቶ ከጸበሉ ጠጥቶ ለዐጼ ዮሃንስ ነግሮ ጥብቅ አሰጠው።፡
የዚህ ጊዜ የጎጃም አልቃሽ ከብቱዋን የተዘረፈች ልብሱዋን የተገፈፈች እንዲህ አለች።፡
በላይኛው ጌታ በባልንጀራዎ
በቅዱስ ሚካኤል በጋሻ ጃግሬዎ
በጽላተ ሙሴ በነጭ አበዛዎ
ጎጃምን ይማሩት ፈሪን አንልዎ”።
ከዚህ በላይ በስፋት የጠቀስኩት የዐጼ ዮሃንስ ወደ ጉጃም ይዘውት የመጡትን የትግሬ ጦር በተመለከተ የፈጸመውን ጥቃት የጠቀስኩበትን ምንጭ፡ “የኢትዮጵያ ታሪክ በአለቃ ተክለ ጊዮርጊስ” በ2002 ዓ. ም. በዶክተር ሥርግው ገላው ሐተታከታተመው መጽሃፍ በገጽ 163-165 ላይ የሰፈረውን ነው። ይህ ከላይ በስፋት የጠቀስኩት የዐጼ ዮሃንስ ዘመን ግፍ፤ የትግሬ ወታደሮች በዚያ በራቀውና ክርስቲያኑ ንጉስ በሚባለው በዮሃንስ ጊዜ እንኳን ምን ያህል ለታቦት፤ ለቤተክርስቲያን ክብር የሌላቸው ነውረኞች እንደሆኑ አንባቢ እንዲያውቅ ነው። እነዚህ ሰዎች ቤተክርስቲያንም ሆነ መስጊድ ሄደው ይጸልዩ ይሆናል እንጂ እንከተለዋለን የሚሉት የክርስትናም ሆነ የእስልምና ስነ ምግባር ህይወታቸውን እንደማይመራ መረዳት ያስፈልጋል። ዛሬ ደግሞ የፋሽስት ርዕዮተዓለም ህሊናቸው የታወሩት የወያኔ ትግሬዎች ከእነሱ ነገድ ውጭ ላለው ህዝብ ህይወት፤ ስሜት ደንታ የሌላቸውና አዲሱ የፋሽስት ሃይማኖታቸው ማናቸውንም ዒ-ሰብዓዊ ድርጊት እንዲፈጽሙ የሚያደርጋቸው መሆኑን ለመግለጽ ነው።
ይህን ጽሁፍ ለመጻፍ መነሻ የሆነኝ ሌላው ምክንያት ምንድነው? ሌላው ይህንን ጽሁፍ ለመጻፍ ያነሳሳኝ ፌስ ቡክ በሚባለው የማህበራዊ መገናኛ አውታር ላይ ሰፍሮ ያየሁትና ቀልቤን የሳበው የአንድ እብሪተኛ የትግራይ ፋሽስት ወጣት ምሁር ጽሁፍ ነው። ይህ ሰው ዘጸዓት ሳቬአድና አናንያ የሚባል በመቀሌ ዩኑቨርሲቲ ውስጥ የሚሰራየሚሰራ ሃኪም ሲሆን አክራሪ የትግራይ ብሄረተኛነት በፈጠረው ስሜት የእብሪት ጽሁፎችን በመጻፍ የሚታወቅ የትግራይ ተወላጅ ነው። ይህ ግለሰብ በትግርኛ ቋንቋ የጻፈው ጽሁፍ ይዘት የወልድያ ፍጅት እንዴት በትግራይ ፋሽስቶች ቀደም ብሎ ተጠንቶበትና ተዘጋጅቶ የተካሄደ መሆኑን አመልካች ስለሆነ ከዚህ በታች በፌስቡክ ገጹ ላይ ያሰፈረውን ሃሳብ ይዘት አንብባችሁ እንድትረዱት አቅርቤዋለሁኝ። እኔ ትግርኛ ቋንቋን ስለማልረዳ ከዚህ በታች የሰፈረውን የትግርኛውን ጽሁፍ ወደ አማርኛ ተርጉሞ የላከልኝ የዘወትር ተባባሪ ወዳጄ አቶ ጌታቸው ረዳ (San Jose, California) ነው። ለዚህ ሁልጊዜ ያልተለየኝ ትብብሩ ምስጋና ይግባው።
የትግራዩ ብሄረተኛ ዘጸዓት በፌስቡክ ገጹ የለቀቀው ጽሁፍ ይዘት ምን ይመስላል? የወያኔ መንግስት በወልድያ ስለ ጀመረው የዘር ፍጅት ምን ይነግረናል?
ይህ ከዚህ በታች ያሰፈርኩት የዘጸዓት ጽሁፍ ግልጽና በማያሻማ መንገድ እንደሚያሳየው የወያኔ መንግስት የወልድያ ወጣቶች የወያኔን ሥርዓት በመቃወም በሰላማዊ መንገድ ስሜታቸውን የገለጹበትን ሁኔታ በጉልበት የምዕራብ ትግራይ አካል አድርጎ በጠቀለለው የወልቃይት ጸገዴ አክባቢ የተነሳው የአማራ ህዝብ እንቅስቃሴ አካል አድርጎ እንደሚመለከተው ያሳያል። የወያኔ መንግስት የአማራ ህዝብ በወልቃይትና ጸገዴ ያልተሳካለትን ትግል ወደ ሰሜን ወሎ በመውሰድ ትግራይን ለማጥቃት እንደተነሳ አድርጎም ቆጥሮታል። ከዚህም የተጠራጣሪነት የፍራቻና የመከበብ ስሜት (siege mentality) በመነሳት በጎንደርና በወሎ ህዝብ ትብብር የሚመራ ኃይል “ወደ ትግራይ እምብርት ወደ ራያ አካባቢ ሠርጎ በመግባት እርኩስ ዓላማውን ለማሳካት እንዳቀደ እና እያቀደ እንዳለ በርካታ መረጃዎች አሉ” ይለናል ዘጸዓት።
Ztseat Saveadna Ananya –January 21, 2018 at 8:21 PM
“በጎንደር እና ዋሺንግተን ዲሲ ተጠንቶ በምዕራብ ትግራይ ላይ ያነጣጠረው የተጠመደው የተስፋፊዎችና የጥላቻ ሓይሎች ዕቅድ በትዕግስተኛው እና አስተዋይ የአካባቢው ሕዝብ ትግል ሊመክን ችሏል። በምዕራብ ትግራይ ያጠመደውና የትግራይን ሕዝብ ህልውና እና ጥቅም የሚጻረረው የዚህ ክፉ ሃይል መሰሪ ዕቅድ አልሰራ ሲለው፤ተስፋ ቢስነትቱን በመቀጠል ‘እኔ ካልበላሁት ልበትነው’ ከሚለው የዶሮ አስተሳሰብ በመነሳት ሁለተኛውን ምዕራፍ ማለትም “ራስን የመግደል’ (ሱሳይዳል) ሙከራ ለማድረግ ወሎ ውስጥ እሳት ለኩሶ ወደ ትግራይ እምብርት ወደ ራያ አካባቢ ሠርጎ በመግባት እርኩስ ዓላማውን ለማሳካት እንዳቀደ እና እያቀደ እንዳለ በርካታ መረጃዎች አሉ።
ያ ከጥቂት ሳምንታት በፊት በ40 የጭነት መኪኖች ተጭነው ከጎንደር የመጡት ከጥቂት የወልዲያ ወጣት ተባባሪዎቻቸው ጋር በመቀናጀት ወልድያ ውስጥ በሚኖሩ ትግሬዎች ላይ የህይወትና የንብረት መጥፋትና ብጥብጥ ምክንያት የሆነበት ምክንያትም ለብዙ ጊዜ ውስጥ ለውስጥ በጥናት ሲካሄድ የነበረው የጥናቱ ምዕራፍ አንድ ነው። የሴራው መሃንዲሶች ቀጣይ ምኞትም ወደ ሰፊው የወሎ አካባቢዎች እና እስከ አለውሃ–ምላሽ አልፎ ወደ ቆቦ እና የመሳሰሉ አካባቢዎች እንዲሁም ወደ ራያ ለመግፋት አቅዶ ነው እየተንቀሳቀሰ ያለው። ትግራይ ውስጥ ያለ ትግሬ በተለይ ከትግራይ ውጭ ያሉ የወሎ አካባቢ እና ደቡብ ትግራይ ያሉ የትግራይ ወጣቶች በደምብ እንዲያስተውሉት የሚገባው ነገር ጉዳዩን በስሜታዊነት ሳይሆን በንቃት፤ ባስተዋይነት በጥበብ ጥቃቱን ሊመክተው ይገባል።”
ይህ የትግራይ አክራሪ ብሄርተኛነት በፈጠረው ፋሽስታዊ አመለካከት አይምሮው የተመረዘው ሰው ወገኖቹ የሆኑት የአጋዚ ጦር አባሎች (የትግራይ ተወላጆች) የወልድያን ህዝብ ተንኩሰው ታቦት በሚገባበት ወቅት ተኩስ በመክፈት የወሎን ተወላጆች ከገደሉና ካቆሰሉ በኋላ የሚከተለውን አስተያየትና ምክር ተጎጂ ለሆነው የወልድያ ህዝብ ሰጥቷል። ይህ ሰው የአጋዚን ጦር ሽፋን እየሰጡ፤መረጃ እያቀበሉ በአድፍጦ ተኳሾች(snipers) ስለሚያስገድሉት የህወሃት አባላትና ደጋፊዎች የክፋት ሥራ አንዳችም ነገር አላነሳም።
Ztseat Saveadna Ananya – 21 January 2018
“የወልዲያ ወጣቶች ሆይ፤ ከአማራ ፖሊስ ጋር ተጋጭታችሁ ፤ ተዳምታችሁ ስታበቁ ከምኑም የሌለበትን፤ ምንም የማያውቀውን፤ አብሯችሁ ክፋ ደጉን ያሳለፈውን፤ ስለንፅሕናው እናንተ እራሳችሁ የምትመሰክሩለትን፤ ጎረቤታችሁ አብሮ አደጋችሁ የሆነውን ንፁህ ወንድማችሁ ትግራዋይ ስለሆነ ብቻ ቤት ንብረቱ ላይ እሳት ስትሰዱ እውነት ለህሊናችሁ ዕረፍት የሚሰጥ ሆኖ ነው? እንደምታውቁት ባህላችን ከሌላ አካባቢ የመጣን “እንግዳ” ማክበር እንጂ “በቤታችን” መናከስ አይደለም። ያማ የኛ አይደለም፤ እንደውም የሰውም አይደለም።
እንደምታውቁት ድምፃዊ ቴድሮስ ካሳሁን ስታድየም አመቻችቶ እንዲዘፍን የፈቀደለት የአማራ ክልል መንግስት ነው– ደግ አደረገ። በተመሳሳይ ሁኔታ ደግሞ ለወልዲያ የጥምቀት በዓል ፖሊስ ያሰማራውም እንዲሁ የክልሉ መንግስትና የከተማው አስተዳደር ነዉ። የከተማው የፖሊስ ኮማንደር እንዳሉትም ጎንደር–በር ላይ ወጣቶች ከስድብ አልፈው ፖሊስ ላይ ድንጋይ መወርወር ሲጀምሩ ስምሪት ላይ የነበረው ፖሊስ ተኩሶ የሰው ህይወት እንዲያልፍ ሆኗል። የአውራው ግጭት ታሪክ ይኸው ነው። ታድያ የትግራይ ተወላጆችን ምን በደሉን ብላችሁ ነው ቤት ንብረታቸው ላይ በጅምላ እሳት የምትሰዱት፤ምንስ በደሉ ብላችሁ ነው እጃችሁ የምታነሱባቸው? ደግሞስ “በመስተዋት ቤት ውስጥ የሚኖር ሰው ድንጋይ መወርወር የለበትም” እንደተባለው ይኽ ሁኔታ ወደ መላ ሀገሪቷ ቢስፋፋ ከመጎዳት የሚያመልጥ አለን? ከጥፋት፤ ከውድመት የሚያተርፍ አለን? ሰከን ማለቱ ለሁላችን ይበጃል።
ሶስተኛ ቡድን ደግሞ አለ– በትግራይ ሕዝብ ጥቅምና ሕልውና ፈፅሞ የማይተኛ፤ የፖለቲካ ርዕዮተ–ዐለሙ፣ ታሪኩና የቀደመም የአሁንም መሰባሰብያው “ፀረ–ትግራዋይነት” የሆነ፤ የጠቅላይ አግላይነትና ተስፋፊነት ባህሪያት የነገሱበት ቡድን። ይህ በዋነኝነት ውጪ በሚኖሩ ሐይሎች የሚዘወር ሲሆን ይህ ቡድን በምዕራብ ትግራይ በኩል ሞክሮ የከሸፈበት ሙከራ በደቡብ ትግራይ በኩል ለመሞከር ነው፤ ለዚሁ ቡድን ወልዲያ መሸጋገርያ መሆኗ ነው።”
የዚህ ጽሁፍ ተከታታይ ክፍሎችን በማከታተል አቀርባለሁኝ። ዋናው ዓላማዬ ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የወያኔ ሥርዓት የተቃዋሚ የፓለቲካ ሰዎች እንደሚነግሩን የኮሚኒስት ቀኖናዊነት የተጠናወተው ወይም ነጻ አመለካከት አለን የሚሉ ምሁራን ወዘተ እንደሚነግሩን ልማታዊ መንግስት አይደለም። ወይም ሃይማኖታዊ ዝንባሌ ያላቸው ሰዎች እንደሚነግሩን ሰይጣናዊ መንፈስ የተጠናወተው መንግስት አይደለም። በእኔ ግንዛቤ ሥልጣን ላይ ያለው መንግስት ትግራይ በሚባል ነገድ ማንነት ላይ የተመሰረተ አክራሪ ብሄረተኛነት መገለጫ የሆነ የፋሽስት ሥርዓት የሚያራምድ፤ የአንድን ትግራይ የሚባል ምርጥ ነገድ የበላይነት የሚሰብክ የፋሽስት መንግሥት ነው ብዬ እሞግታለሁኝ። ይህን የማደርገው በተቃዋሚዎችም ሆነ በህዝባችን ውስጥ የዚህን ሥርዓት ትክክለኛ ተፈጥሮ አለማወቃችን ከፍተኛ የሆነ መስዋእትነት ስላስከፈለን ነው።
ጥር 21 ቀን 2010 ዓ.ም. (29th of January 2018)