
“የተከበራችሁ ሆይ ከፓርላማው ምን ቀራችሁ? ከአማራ ህዝባዊ ኮሚቴ የተሰጠ ማስገንዘቢያና ማሳሰቢያ‼ የተከበራችሁ በአማራን ህዝብ ስም አብንንም ሆነ አማራ ብልጽግናን ወክላችሁ በፌደራል ፓርላማና በአማራ ክልል ምክር ቤት የገባችሁ ወገኖቻችን፦ እንደምታውቁት የአማራ ህዝብን ድምጽ በመወከል በፌደራልና በክልል ምክር ቤት በአማራ ህዝብ ላይ በሚደረጉ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ ውሳኔዎች ላይ ድምጽ ለመስጠት እና የውሳኔ አካል ለመሆን የህዝብ እንደራሴ ሆናችሁ የአማራን ህዝብ መወከላችሁ ሚናችሁ ከፍተኛ ሊሆን እንደሚገባ እሙን ነው። መቼም ወደ ምክር ቤቶች ህዝብን ወክሎ መግባት፣ ትልቅ ስራ የሚሰራበት መልካም እድል እንደሆነ ለእናንተ የተሰወረ አይደለም። የእኛ ጥያቄ በዚህ መልካም እድል እናንተ ከዚህ ቀደም ምን ሰራችሁበት? ከዚህ በኋላስ ምን ልትሰሩ ታስ…ባላችሁ? የሚለው ነው? እንደምታውቁት የህዝብ ተወካዮች በፓርላማ የሚሰየሙት በአንድ ሀገር ውስጥ ያለው መንግስት የሲቪል መንግስት ነው ተብሎ ሲታሰብ ነው። ሆኖም በአሁኑ ወቅት እናንተ ወከልነው የምትሉት የአማራ ህዝብ በኦነጋዊው የጦር ጀነራሎች በሚታዘዘው መከላከያ ሰራዊት መዳፍ ስር ወድቆ በወታደራዊ የግዛት አስተዳደር ቁም ስቅሉን እያየ ያለ ህዝብ ነው። መረጠን የምትሉት የአማራ ህዝብ በወታደር ጫማ እየተረገጠ፣ ከመንግስት ጋር በጥይት ቋንቋ እየተነጋገረ በየእለቱ በሚሞትበት ሁኔታ የእናንተ በፓርላማ ወንበር መሰየም ፋይዳው ምን ይመስላችኋል? ከዚህ ሁኔታ የእናንተ በፓርላማ መገኘት የኦነጋዊው መንግስት የአማራ ገጽታ እንዳለው ከማስመስከር ውጭ ለአማራ ህዝብ የሚፈይደው ነገር ምንድን ነው? ወይንስ ህዝቡ በምንም አይነት መከራ ውስጥ ቢኖር ዋናዉ ቁም ነገር የእናንተ በፓርላማ የተቀመጡ “የተከበሩ” መባል ይመስላችኋል? የአማራን ህዝብ እያሳደደ በሚያርደው ኦነጋዊ ስርዓት ፓርላማ ውስጥ ከዚህ ቡኋላ መቆየት ራስን የመናቅ አሳፋሪ ተግባር እንደሆነ ልትረዱት ይገባል። ኦነጋዊው አስተዳደር የሚያሽከረክረው እናንተ የተሰየማችሁበት ፓርላማ ለአማራ ህዝብ መከራ መፍትሄ ሊሰጥ ቀርቶ ችግሩን መስማት የማይፈልግ እንደሆነ የአደባባይ ሀቅ ነው። እናንተም ወከለን የምትሉትን የአማራ ህዝብ ውርደት፣ ፍጅት፣ እገታ፣ ጥቂት ጠበቅ ባለ ሁኔታ አንስታችሁ አታውቁም። ከመካከላችሁ በጣም ጥቂት የአማራ ህዝብ ችግር አንስተው ሊሞግቱ ሲሞክሩ ፓርላማው የሚስቀው ሳቅ ለወከላችሁት ህዝብ የሚቀርብ የክብር መስዋእት እንዳልሆነ የሚጠፋችሁ አይመስለንም። ድፍን ሶስት አመት በፓርላማ ስትቀመጡ የአማራ ህዝብ በየቀኑ እየታረደ፣ በየደቂቃው እየተፈናቀለ፣ በየሰዓቱ እየተሰደደ ነበር። ይህን ለማሰቀረት ያደረጋችሁት ጥረትና ተጽዕኖ እዚህ ግባ የሚባል አልነበረም። እናንተ “የተከበሩ” እየተባላችሁ በምትጠሩበት ፓርላማ የህዝብ ስቃይ መሳቂያ እና መሳለቂያ ነው። በዚህ ሁኔታ መከበራችሁ ወዴት ነው? የህዝብ ፍጅት ፣ ስደት እና እገታ ሳይገታ ጭራሽ መላው የአማራ ህዝብ በወታደራዊ አስተዳደር ስር ወድቆ ጥይት እና ባሩድ ከመንግስት ጋር የመግባቢያ ቋንቋ ሆኖ ጸበለተኛ ላይ ሳይቀር ቦምብ ሲወርድ ፓርላማ የምትቀመጡት ምን ቀረን ብላችሁ ነው? ከዚህ በኋላ ፓርላማ መቀመጣችሁ የኦነጋዊውን መንግስት ዙፋኑንን ከመሸከም ያለፈ ለአማራ ህዝብ አንዳች ትርጉም የለውም። ከዚህ በኋላ ፓርላማ መቀመጣችሁ በህዝባችሁ የሀዘን ድንኳን ውስጥ ለመደነስ የመድፈር ያህል ነው። ለመሆኑ እናንተ ወከለን በምትሉት የአማራ ህዝብ ላይ የሚወርደው መከራ ከኢትዮጵያ ብሄሮች በአንዱ ላይ ወርዶ ቢሆን ኖሮ ይህን ያህል አመት ህዝቡን እያፋጀ፣ ጭራሽ ለወታደራዊ አስተዳደር አሳላፎ ሰጥቶ ፓርላማ የሚቀመጥ የሌላ ብሄረሰብ ወኪል ያለ ይመስላችኋል? የዚህን ጥያቄ ትክክለኛ መልስ ለማግኘት ከሶስት አመት በፊት እናንተ ዛሬ በተቀመጣችሁበት ፓርላማ የሆነውን ታሪካዊ ክስተት አጢኑ። ከሶስት አመት በፊት የትግራን ህዝብ ወክለዉ ፓርላማ ገብተው የነበሩ አቻዎቻችሁ ህዝባቸው በኦነጋዊ አስተዳደር ተበደለ ብለው ሲያስቡ ፓርላማውን ለቀው ውልቅ ያሉት ጨርቄን ማቄን ሳይሉ ነው። እነዚህ የትግራይ ወገኖቻችን ይህን የህዝብ ወገንተኝነታቸውን ያሳዩት ህዝባቸው እንደ አማራ ህዝብ በስካቫተር ተቀብሮ፣ ሶስት አመት ሙሉ ስደተኛ ጣቢያ ተቀምጦ፣ በእገታ እየተያዘ በሚሊዮን የሚቆጠር ዋጋ ተጠይቆበት፣ አዲስ አበባም አትገባም ተብሎ፣ በሸገር ከተማ በላቡ ደክሞ የሰራው ቤቱ በጅምላ እየፈረሰበት፣ በቃሪያ ጥፊ ተመትቶ የውርደትን ጥግ አይቶ አይደለም፣ ይልቅስ አዝማሚያው አላማረንም፣ ባለስጣኖቻችን ተለይተው ተሰደቡ ወዘተ ብለው ነው። እነዚህ የትግራይ ህዝብ ተወካዮች የወከሉት ህዝብ እና እናንተ የወከላችሁት ህዝብ በመንግስት ዘንድ የሚሰጠውን ክብር ልቦናችሁ ይመዝነው! በስተመጨረሻ ደግመን ልናሳስባችሁ የምንወደው ነገር ቢኖር ከዚህ በኋላ ፓርላማ መቀመጣችሁ ትርጉም የሚሰጠው ለኦነጋዊው ስርዓት እንጅ በወታደራዊ አስተዳደር ግዛት ውስጥ ላለው የአማራ ህዝብ እንዳልሆነ ነው። ህዝባችሁ በወታደራዊ አስተዳድር ውስጥ ሆኖ እናንተ ሲቪል ዜጎች ፓርላማ መገኘታችሁ ፓርላማ መግባታችሁ ራሱን ትርጉም የሌለው ጉዳይ ያደርገዋልና በጊዜ ውግንናችሁን ከህዝብ በኩል እንድታደርጉ በወገናዊ አክብሮት ልናሳስባችሁ እንወዳለን። ከዚህ በተቃራኒው ከሄዳችሁ ውግንናችሁ የአማራን ህዝብ እንደደመኛ ጠላቱ ለሚያየው ኦነጋዊ አስተዳደር መሆኑን ልናሳውቃችሁ እንገደዳለን። የክብሩን መንገድ እንዲያስመለክታችሁ እንመኛለን! የአማራ ህዝባዊ ኮሚቴ ህልውናችን በክንዳችን! የአማራ ህዝብ ትግል ያሸንፋል! https://youtu.be/bLgnerLn4oE
Source: Link to the Post