የኢኮኖሚክስ መምህርና ጸሓፊ
(ሸክም የበዛበት ትውልድ፡ 2009 እና
የምሥራቃዊት ኮከብ፡ 2010 መጻሕፍት አዘጋጅ)
ፖለቲካና ሥልጣን በሀገራችን የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው፡፡ ትንሽ ሕዝብ – ሕዝብ፣ ኢ-ዲሞክራሲያዊ፣
አፋኝ፣ ጨቋኝ – – – ወዘተ ሌላው ደግሞ ሕገ መንግሥታችን፣ መንግሥታችን፣ ድርጅታችን – – – ወዘተ ከማለት
በዘለለ ትርጉም ያለው የፖለቲካ ዕውቀት፣ አቅም፣ ስብዕናና ብቃት የሌለው ሰው ፖለቲካ ውስጥ ይገባና ፖለቲከኛ
ሳይኾን ፖለቲከኛ ይባላል፡፡
ሁለተኛውን ማሳያ – ከሥልጣን አንጻር ያለው ነው፡፡ በሀገራችን ሰላማዊ ትግል በሚያካሂዱና በገዥው ፓርቲ –
ተመሳሳይ ኹኔታዎች ያሉና የሚኖሩ ቢኾንም በዋናነት በሁለት ነጥቦች ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ አንዱ በሌላው፤
አንደኛው በሌላኛው ላይ – በአንደኛው ውስጥ ቢኖርም – ተፎካካሪ ፓርቲዎች በቲፎዞ ፖለቲካ – የገዥው ደግሞ
የሹመት ፖለቲካ ነው፡፡
I. የቲፎዞ ፖለቲካ
የቲፎዞ ፖለቲካ መሰረቱ ቲፎዞ ነው፡፡ ብዙ ቲፎዞ ያፈራ የፖለቲካ ፓርቲ አባልና መስራች መሪ ይባላል፡፡ ይኾናል፡፡
ይህ ከመነሻው ፓርቲ ሲመሰረት ሀሳብህ ምንድነው? ሳይኾን ይህንን ያክል ሰው አስፈርም ይባላል፡፡ ከዚህ
ይጀምራል፡፡
ፓርቲው ከመነሻው ትርጉም ባለው ሀሳብ ለምን? በምን? እንዴት? በምን ኹኔታ? ሳይጠየቅ፣ ሳይጨነቅ፣
ሳይመረመር፣ ሳይመልስ – በአንድ ሰው ጸሓፊነት – በቲፎዞ ስብሰባ ሊቀ መንበር ይኾናል፡፡ ቲፎዞ ሰብስቦ ሊቀ
መንበር የኾነው የቲፎዞው አሰባሳቢ የግል አቋም – የፓርቲው ይኾናል፡፡
የሱ የማንበብ አድማስ ጠቦ የተቀመጠ ነጥብ ለቲፎዞው እምነት ይኾናል፡፡ ሀ – ብሎ የቲፎዞ ፖለቲካ የሚጀምር
ከዚህ ይኾናል፡፡ ይቀጥላል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤ ብሎ ይጠራል፡፡ የጠራቸው ሰዎች እሱ የሚሰጣቸውን ሰዎች ስም
ይጠራሉ፡፡ እሱ በቀላሉ ያለ ማንም ተቀናቃኝ መሪ ይባላል፡፡ ሌሎችም እንዲሁ መሪዎች ተብለው መጠራት
ይጀምራሉ፡፡ ያለ ትርጉም ያለው ትውውቅና የሀሳብ ሙግት ለ – ብሎ ይቀጥላል፡፡
ተጠሪዎች እርስ በራሳቸው ስለማይተዋወቁ ጠሪ ማን – ማንን መምረጥ እንዳለበት በጓዳ ስሌት አስልቶ ይገባል፡፡
አመራሮች ተብለው ሌሎች ይመረጣሉ፡፡ መራጮችም ሳይተዋወቁ በጠሪ አማካኝነት ተጠሪዎች – መሪዎችን
ይመርጣሉ፡፡ ሐ – ብሎ ይቀጥላል፡፡ መሪዎቻችን እንዳይሉ አያወቋቸው – በሉ እንዳይባሉ ማን ደፍሮ ይላል?
ጠሪ/አሰባሳቢ ግን መሪያችን ይባላል፡፡ መ – ይቀጥላል፡፡
ጠሪ/ሰብሳቢ ወደ ተጠሪዎች እንዳልሄደ አኹን ተጠሪዎች ወደ ጠሪ ካልሄዱ በቀር ጠሪ ይርቃል፡፡ ተጠሪዎች
በጠረጴዛ ዙሪያ ይሰባሰባሉ፡፡ ጠሪና የተመረጡ አመራሮች ሳይስማሙ ሲቀሩ ተጠሪዎች ቀድመው ጉዳዩን ሳይሰሙ
ውግንናቸው ከጠሪ ይኾናል፡፡ አመራሮች ወጣ ብለው ድምጽ ሲያሰሙ ጠሪ ስም ማጥፋት ይጀምራል፡፡ ሠ – ብሎ
ሂደቱ ይቀጥላል፡፡
የቲፎዞ ፖለቲካ በሀገራችን በአጭሩ ለመመሰል እግር ኳስ ጥሩ ምሳሌ ነው፡፡ ሰዎች ኳስን ሲደግፉ እንደኹኔታው
ነው፡፡
ብሔራዊ ቡድናችን ከሌላ ሀገር ብሔራዊ ቡድን ጋር ሲጫወት ሀገራችንን እንደግፋለን፡፡ ቡድናችን አቅምና ብቃት
ስላለው – የሌላው ሀገር ብሔራዊ ቡድን አቅምና ብቃት ስለሌለው ሳይኾን እንዲሁ በሀገራዊነት እንደግፋለን፡፡
የፋብሪካችን ቡድን ከኾነ – የፋብሪካችን ስለኾነ እንደግፋለን፡፡ የከተማችን ከኾነ እንዲሁ – የሰፈራችን ካለበት
አልያም ቤተሰባችን ካለበት እንዲሁ ነው፡፡
የቲፎዞ ፖለቲካም እንዲሁ ነው፡፡ ከባቢያዊነትን ስለሚያቀነቅኑ፣ ሀገራዊነትን ስለሚያቀነቅኑ፣ ምሁራን
ስለሚባሉ፣ ምሁራን ስለኾኑ፣ ያካባቢያችን ሰዎች ስለኾኑ፣ ታዋቂ ስለኾኑ፣ ቤተሰቦቻችን ስለኾኑ፣ ሌላውን
2
ስለምንቃወም – – – ወዘተ ፖለቲካ ውስጥ እንገባለን፡፡ ብዙዎች ፖለቲካ ውስጥ የምንገባው ትርጉም ባለው
መልኩ በምክንያትና በዕውቀት ላይ ተመስርተን አይደለም፡፡
አመራር የሚመረጠው እንዲሁ በቡድን ቅስቀሳ፣ በድለላ፣ በሴራ፣ በከባቢያዊነት፣ በታዋቂነት፣ በተናጋሪነት፣
በቀስቃሽነት – – – ወዘተ እንጂ በአቅምና ብቃት በትርጉም ያለው የፖለቲካ ዕይታ አይደለም፡፡
የቲፎዞ ፖለቲካ በቲፎዞ ይመራል፡፡ የተሻለና ብዙ ቲፎዞ ያለው የፖለቲካ መሪ ይባላል፡፡ ብዙ አጨብጫቢና እጅ
አውጭነት ዋነኛ መስፈርት ይኾናሉ፡፡ ለዚህም ነው – ከሕገ ደንብ የዘለለ ግለሰባዊነት ሊሸከም የሚችል –
ከግለሰቦችና ቡድኖች በላይ የኾነ የፖለቲካ እንቅስቃሴ በአብዛኛዎቹ የሀገራችን ተፎካካሪ ፓርቲዎች የሌለው፡፡ ቲፎዞ
- የእግር ኳስ ቡድን ቲፎዞ – አንደኛው በማሸነፉ ብቻ አይደለም የሚደሰተው፡፡ ከአሸናፊነቱ በላይ የሌላው ተሸናፊነት
ከፍተኛ ደስታ ይሰጠዋል፡፡ የቲፎዞ ፖለቲካም እንዲሁ ነው፡፡
II. የሹመት ፖለቲካ
የሹመት ፖለቲካን በሁለት ከፍለን መመልከት እንችላለን፡፡
ይኸውም፡-
2.1 ህልው ሹመት
2.2 ህልው ያልኾነ የውክልና ሹመት
የሹመት ዋነኛ መመዘኛ በገዥ ሥርዓታት ታማኝነት ነው፡፡ ታማኝነት ቀዳሚውን ቦታ ይይዛል፡፡ ቡድናዊነት ውስጥ
መታመን ቁልፍ ነገር ነው፡፡ የምትታመነው ለሿሚህ ነው፡፡ ሿሚህ ቡድን ነው፡፡
የታዳጊ ሀገራት የሥልጣን ፖለቲካ ወደ ተቋማዊነት አልተሸጋገረም፡፡ ሀገራዊ ማዕቀፍ ሳይኖረው ሊሸጋገርም
አይችልም፡፡ የተሿሚ ታማኝነት ሀገራዊ ማዕቀፍ ባለባቸው ሀገራት – ለሀገራዊ ማዕቀፍ ነው፡፡ አቅራቢያቸው
ፓርቲያቸውን ወዴት? እንዴት? የሚሉ አይደሉም፡፡ ተቋማዊነቱ ይገዛቸዋል፡፡ ፍርሃት የለም፡፡ ሀገራቸውን
እስከጠቀመ ድረስ የበላያቸውና በአቅራቢያቸው ያለውን ይሞግታሉ፡፡ ክብር እንጂ ፍርሃት የለባቸውም፡፡ በህልው
ሹመት – ተሿሚ ህልውናውን ጠብቆ ይመራል፡፡
በህልው ሹመት ተሿሚ የሚመረጠው ባለው ብቃት፣ አቅም፣ ፍላጎት፣ ስብዕናና ተግባር ላይ በመመስረት ነው፡፡
በህልው ሹመት፡ ሹመት ወደ ተሿሚ ይመጣል እንጂ ተሿሚ ወደ ሹመት አይሄድም፡፡
እነዚህም ትርጉም ባለው መልኩ በአደባባይ የታወቁ የማንነቱ መገለጫዎች ናቸው፡፡ ህልው ተሿሚ በችሎታው –
አጋሮቹ ብቻ ሳይኾኑ ተቀናቃኞቹ ሳይቀሩ የሚመሰክሩለት ነው፡፡ ይህም በመኾኑ በአብዛኛው ሕዝብም ኾነ በተለያዩ
አካላት እውቅናና ክብር የሚቸረው ይኾናል፡፡
ተሿሚነት ለሥልጣኑ መቀመጫና ማግኛ መሣሪያ ብቻ ኾኖ ያገለግላል፡፡ በተሿሚና በሿሚ መሐከል የሚኖረው
ግንኙነት ኹሉ በሀገራዊ ማዕቀፍ – ተቋማዊነት የሕግ አግባብ ይገዛል፡፡ መገዛቱንም የግድ የሚል ይኾናል፡፡
ሁለተኛው፡- ህልው ያልኾነ የውክልና ሹመት በአንጻሩ ተሿሚ ህልውና የለውም፡፡ እሱ ወኪል ነው፡፡ ጠቅላይ
ሚኒስትር፣ ፕሬዝደንት፣ ሚኒስትር – – – ወዘተ ቢባል እሱ አይደለም የሚኾነው፡፡ ሹመቱ በሱ በኩል ያልፋል
እንጂ እሱ እውነተኛ ሹመኛ አልያም ህልው ተሿሚ አይደለም፡፡ ወኪል ስለኾነ የወኪልነት ሥራ ብቻ ይሰራል፡፡
ውክልናው የሞያ፣ የጾታ፣ የመደብ፣ የዕምነት፣ የአካባቢ፣ የኾነ ሕብረተሰብ ክፍል – – – ሊኾን ይችላል፡፡ ህልው
ያልኾነ የውክልና ተሿሚ የራሱን ህልውና ለውክልና ሲል የሚሸጥ ነው፡፡ አንድ ሰው አቅምና ብቃት ሳይኖረው
ለውክልና ሲባል ይገባል፡፡
አቅምና ብቃት የሌላቸው ህልው ያልኾኑ ውኩል ሹመኞች ፍጹም ታማኝነታቸው ለሿሚያቸው ይኾናል፡፡
ምክንያቱም ቦታው ተገብቸውና ስለሚችሉ እንዳልያዙት ስለሚያውቁና ስለሚታወቅ ፍጹም ታማኝነታቸው
ለሿሚያቸው መኾኑ አያጠራጥርም፡፡
እንዲህ ዓይነት ሰዎች ለበላያቸው ብቻ ሳይኾን በታች ባለና ከላይ ጋር ትስስር ባለው ግለሰብ ብቻ ሳይኾን አቅምና
ብቃት በሚኖራቸውና ባላቸው የበታች አመራሮችና ባለሙያዎች ኹሉ እንደተፈለገ የሚሽከረከሩ ናቸው፡፡
በውስጣቸው የበታችነት ስሜት (inferior complexity) ስለሚፈጠር – ማይሰሩና ማያሰሩ ይኾናሉ፡፡
ሲጀመርም በማይገባውና በማይችለው ቦታ የሚቀመጥ ሰው በመዠመሪያ ትርጉም ያለው ሕይወት የማይኖር፤
ራሱን የማያውቅ ሰው ነው፡፡
3
በተፈጥሮ ሳይኾን በተፈጥሯዊ ሂደት (not by nature but ACCORDING to nature) ጠንካራ ደካማን
ይገዛል፤ ዝናብ ከላይ ወደ ታች ይዘንባል፤ የተሻለ ሌሎችን ይመራል፡፡
ነገር ግን በሥልጣን ፖለቲካ ውስጥ የሚዳክሩት አብዛኛዎቹ ታዳጊ ሀገራት በመሪ አዘቅጥ (በጠንካራ
ተማዊነት ውስጥ የተሸሸጉትም የበለጸጉ ሀገራት ቢኾኑ በመሪ አዘቅጥ ውስጥ እንዳሉ ሳይዘነጋ) ውስጥ
መኾናቸው የአደባባይ ምሥጢር ቢኾንም ‘ዐይናችሁን ጨፍኑ እናሞኛችሁ’ ፍጡር ፈጣሪን፤ የመሪነት አቅም፣
ችሎታ፣ ስብዕናና ብቃት የሌለው የመሪነት አቅም፣ ችሎታ፣ ስብዕናና ብቃት ያለውን ይመራል፤ ዝናብ ከላይ ወደ
ታች ሳይኾን ከታች ወደ ላይ ይዘንባል ብለው ደረቅ ኢ-ተፈጥሯዊና አመክንዮ አልባ የኾነ ክርክር የሚገጥሙ
መኾናቸው የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡
በአደባባይ የሚታወቁ የመሪነት አቅም፣ ችሎታ፣ ስብዕና፣ ብቃት – – – የሌላቸውና እንደሌላቸውም ለዓመታት
ያስመሰከሩ ሰዎች ‘መሪ’ ተብለው ሲጠሩ መስማት የተለመደ ነው፡፡
አንድ ሰው ህጋዊ ባልኾነ መንገድ በአራጭ ሀብት ሲያፈራ ሙሰኛ እንደሚባለው ኹሉ እነዚህም ምንም እን
ህጋዊ በሚመስልና በኾነ መንገድ ‘መሪ’ የሚባሉ ቢኾንም ትርጉም ባለው መልኩ ብንመረምረው የሥልጣን
ሙሰኞች ናቸው፡፡
የመሪነት አቅም፣ ችሎታ፣ ስብዕና፣ ብቃት – – – ሳይኖራቸው ‘መሪ’ የሚባሉ ግለሰቦች በሙሉ የሥልጣን
ሙሰኞች ናቸው፡፡ ምክንያቱም ሳይገባቸው በማይገባቸው ቦታ ላይ ለመቀመጥ የፈቀዱትና የተፈቀደላቸው በአንጻሩ
የነሱ እዛ መቀመጥ ለአስቀማጮች ፋይዳ ያለው ከመኾኑም ባሻገር ባሪያና አሽከር ለመኾን የፈቃደኝነት ማረጋገጫ
በመኾኑ ነው፡፡
ብዙ ታዳጊ ሀገራት በቅኝ ግዛት በወደቁና ከቅኝ ግዛት ተላቀቁ በተባሉበትና በተላቀቁበት ጊዜ ታዳጊ ሀገራት –
መሪዎች የተባሉ ነበሯቸው፡፡ ነገር ግን መሪዎቹ በስም እንጂ እውነተኛ መሪዎች ሌሎች መኾናቸው
ይታወቃል፡፡ የመባልና የመኾን አጽንዖት ትርጉም ባለው መልኩ መመልከት አስፈላጊነትን ያመላክታል፡፡
ስለውክልና ሹመት በተነሣ ቁጥር ከማይዘነጉት ቁልፍ ጉዳዮች አንዱ ህልው ያልኾነ ውክልና/በውኩል/ ሹመት
ፖለቲካ – ታማኝነት ቁልፍ ጉዳይ እንደኾነ ነው፡፡ ይቺ ታማኝነት ግን በሌሎች ቦታዎች ላይ እንዳለችው ዘላቂና ረጅም
ጊዜ የምትቆይ፣ የማትለዋወጥ፤ በግል ስብዕና ላይ የምትመሰረት – ከውስጥ ወደ ውጭ የምትወጣ ታማኝነት
ሳትኾን ከጊዜና ከወቅት ጋር እየተያየች የምትሄድ፤ ከውጭ ወደ ውስጥ የምትገባ – የኃይል ሚዛንን መሠረት
የምታደርግ ቅድመ አስረ አንደኛው ሰዓት ብቻ መኾን ማስተዋል በእጅጉ ያስፈልጋል፡፡
ህልው ያልኾነ ውኩል ሹመት አንጋሾች (king makers) ሊኖሩት የግድ ነው፡፡ ነጋሾች በአንጋሾች (king
makers) ቡራኬ – በተፈላጊው ሰዓትና ኹኔታ ሊነሡና ሊወድቁ እንደሚችሉ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡
ሲነሡና ሲወድቁም ማንም ለምን; የት ገቡ; ብሎ አይጠይቅላቸውም፡፡
የታማኝነት ውስጠ ወይራነት የምትመጣው አንጋሾች (king makers) የኃይል ሚዛናቸው እስከተጠበቀ ድረስ
ብቻ ነው፡፡ ነጋሾችም /ህልው ያልኾነ ውኩል ተሿሚ/ እችን ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ አንጋሾች (king makers)
በአንጻሩ ለህልውናቸው ሲሉ ከነጋሾች በላይ እጅጉን ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ አስረ አንደኛው ሰዓት ደርሶ አንጋሾች
(king makers) የኃይል ሚዛናቸው ቢዛባ የነጋሽ (ህልው ያልኾነ ውኩል ተሿሚ) ታማኝነት አብሮ እንደሚዛባ
የታወቀ የሥልጣን ፖለቲካው ጨዋታ (game) አካሄድ ነው፡፡ ለዚህ ነው – በርካታ ህልው ያልኾኑ ውኩል
ተሿሚዎች በተለያየ ወቅት ፍጹም የተለያዩ ሥርዓታትንና ፍጹም የተለያዩ ቦታዎች ላይ ሲያገለግሉ የምንመለከተው፡፡
በመኾኑም ህልው ያልኾነ ውኩል ሹመት ታማኝነት ማለት እንደሌላው ቦታ ከውስጥ ወደ ውጭ የሚወጣ – በራስ
ስብዕና ላይ የተመሠረተ ሳይኾን ከባቢያዊና ወቅታዊ ኹኔታን ብሎም የኃይል ሚዛንን መሠረት በማድረግ ከውጭ
ወደ ውስጥ የሚገባ ነው፡፡ በበርካታ ታዳጊ ሀገራት የውክልና ተሿሚ ስብዕና መዋዠቅና ዝቅጠት መሠረቱም ይኸው
ነው፡፡ ለነገሩ – ለራሱ ታማኝ ያልኾነ ሰው ለሌሎች ፍጹም ታማኝ ይኾናል ብሎ መጠበቅ ከሞኝነት በላይ እጅጉን
የላቀ ጅልነት ነው፡፡
ባለሥልጣንነት በመኾንና በመባል ይለያያል፡፡ መባል መኾን አይደለም፡፡ ላይኾንም ይችላል፡፡ በመኾን ውስጥ
መባል ባሕሪያዊ ነው፡፡ ባለመባል ውስጥ ግን የጀርባ መባሎች ይኖራሉ፡፡ እነዚህም አንጋሾች (king makers)
ይባላሉ፡፡
4
የአንድ ሥርዓትን ማንነት ለማወቅ ወረቀት ላይ የሰፈረው ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ በሥርዓቱ ዙሪያ ያሉት
ግለሰቦች/ቡድኖች እነማን ናቸው? ምን ያምናሉ? ምን ይሰራሉ? ስብዕናቸው ምን ይመስላል? ከዚህ ቀደም ምን
ታሪክ አላቸው? ለምን መጡ? – – – የሚሉ ጥያቄዎች በዝርዝር መመልከት ያስፈልጋል፡፡
አቅምና ብቃት ያላቸው ግለሰቦች፣ አርቀው የሚያስቡ፣ ከሳጥን ውጭ (out of box) ማሰብ የሚችሉ፣ ህልው
ሹመኞች ያሉበት፣ በዲሞክራሲ የሚያምኑና የሚታመኑ፣ ሐቀኞች – – – በአብዛኛው ያሉበት ሥርዓት – ሥርዓቱ
እንደሥርዓት አቅምና ብቃት ያለው፣ አርቆ የሚያስብ፣ ከሳጥን ውጭ (out of box) የሚያስብ፣ ህልው ሥርዓት፣
በዲሞክራሲ የሚያምንና የሚታመን፣ ሐቀኛ – – – ሥርዓት ሲኾን፤
በአንጻሩ በሥርዓቱ ውስጥ ያሉት አብዛኛዎቹ ግለሰቦች ህልው ያልኾኑ ውኩል ሹመኞች፣ አቅምና ብቃት
የሌላቸው፣ ከሳጥን ውጭ (out of box) የማያስቡ፣ በዲሞክራሲ ማያምኑና ማይታመኑ፣ ሐሰተኞች፣ ሙሰኞች፣
አስመሳዮች – – – የበዙበት እንደኾነ ሥርዓቱ እንደሥርዓት ውኩል እንጂ ህልው ያልኾነ፣ አቅምና ብቃት የሌለው፣
ከሣጥን ውጭ (out of box) ማያስብ፣ በዲሞክራሲ ማያምንና ማይታመን፣ ሐሰተኛ፣ ሙሰኛ፣ አስመሳይ – –
- ሥርዓት ይኾናል፡፡
የማንኛውም ሀገር መንግሥት ሕዝቡን እንደሚመስል ኹሉ አንድ ሥርዓትም እንዲሁ በውስጡ ያሉትን የሥርዓቱን
አንቀሳቃሾች ይመስላል፡፡ ስለኾነም ሥርዓትን ለማወቅ ቀላሉ መንገድ የሥርዓቱ አንቀሳቃሾች እነማን ናቸው? ምን
ዓይነት ስብዕና አላቸው? ብሎ በማጥናት ሥርዓቱን በርግጠኝነት ማወቅ ይቻላል፡፡
እዚህ ላይ ጥንቃቄ የሚያሻው የሥርዓቱ አብዛኛዎችን ማግኘት አስፈላጊ መኾኑ ነው፡፡ የጥቂት ግለሰቦች ማንነትና
ስብዕና የኹሉም ሊኾን አይችልም፡፡ የአብዛኛው ግን በርግጠኝነት የሥርዓቱ ነው፡፡ ያለነሱ ሥርዓቱ የለምና – እነሱ
የሥርዓቱ ህልውና ማሳያ ናቸው፡፡
“Most of the real politics is done in a space where we are spectators. It is the
sphere of professionals not amateurs.” (pp. 11 – Gerry stoker ፡ Why politics matters –
2006) በኛ ሀገር ኹኔታ ግን ጀማሪዎች (amateurs) እንደባለሙያ (professionals) የሚታዩበት ኹኔታ
እጅጉን የጎላ ለመኾኑ አያጠያይቅም፡፡
ስለኾነም የሥልጣን ፖለቲካን ወደ ፖለቲካ ማሳደግና ማበልጸግ አልቻልንም፡፡ የእውነታ ፖለቲካን (real
Politics) ከእውነት ፖለቲካ (truth Politics) ጋር አብሮ ማስኬድ አልተቻለም፡፡ በዚህም በሀገር ኹለንተናዊ
ሂደት መኾን የነበረበት እየኾነ ካለው ጋር ማጣጣም፤ ጽንሰ ሀሳብን ከተግባር ጋር ማቀራረብ አልተቻለም፡፡
(ከ“ሸክም የበዛበት ትውልድ” – 2009 ዓ.ም – ገጽ 124 – 136 የተወሰደ) ፈጣሪ ሀገራችን ነጻ ፍቃድን የኹሉ ነገር
ማዕከል ወደ ሚያደርግ የዕሳቤ ሂደት ትገባ ዘንድ ይርዳን!
ቸር እንሰንብት!