
#የችሎት መረጃ ፍርድ ቤቱ በጋዜጠኞቹ በእነ መስከረም አበራ ቴዎድሮስ አስፋው እና ዳዊት በጋሻው ላይ 15 ክስ የመመስረቻ ቀናትን ለአቃቤ ህግ ፈቀደ! ግንቦት 18 ቀን 2015 ዓ.ም… አሻራ ሚዲያ ፣ ዛሬ ግንቦት 18/2015 ዓ/ም የፌደራሉ ክፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ጊዜ ቀጠሮ ችሎት የቀረቡትና በአራት የተለያየ መዝገብ የተከሰሱት እስረኞች ላይ የክስ መመስረቻና የምርመራ ጊዜ ለአቃቤ ህግና ለፖሊስ ሲፈቀድ የተቀሩት በዋስ እንዲወጡ ተወስኗል፡፡ በዚህም በእነ መስከረም አበራ መዝገብ የተከሰሱት ሶስት ተከሳሾች ጋዜጠኛ መስከረም አበራ ፣ ቢሰጥ ተፈራና ሳሮን ቀባው ላይ ፖሊስ የምርመራ መዝገብ አጠናቆ በዛሬው እለት አድርሶኛል ያለው አቃቤ ህግ ለክስ መመስረቻ የ15 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ይሰጠኝ ብሏል፡፡ በተመሳሳይ በእነ ዳዊት በጋሻው መዝገብ የተከሰሱት ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻውና ቴዎድሮስ አስፋው ላይ ፖሊስ የክስ መመስረቻ የ15 ቀን ጊዜ እንዲሰጠው ጥያቄ አቅርቧል፡፡ በእነ ዳዊት አባቡ መዝገብ በቀረቡት 4 ተከሳሾች ላይ ማለትም በዳዊት አባቡ ፣ በቴዎድሮስ ተሾመ ፣ በአንደበት ተሻገርና በማስረሻ እንየው ላይም በተመሳሳይ 15 የክስ መመስረቻ ቀናትን ጠይቋል፡፡ በአራተኛ መዝገብ በሚገኙት በመንበር አለሙ ፣ በሲሳይ መልካሙና በገብረዓብ አለሙ ላይም አቃቤ ህግ የ15 ቀን የክስ መመስረቻ ጊዜ ይሰጠኝ ብሏል፡፡ የተከሳሽ ጠበቆች በበኩላቸው አቃቤ ህግ ክስ ለመመስረት ያቀረበው የጊዜ ይሰጠኝ ጥያቄ ህጋዊ መሰረት እንደሌለው በማንሳት መከራከራቸውን ሮሃ በችሎት ተገኝታ ተከታትላለች፡፡ ጠበቆቹ“መዝገቦቹን አቃቤ ህግ ከፖሊስ ጋር ሲመራቸው ስለነበር ቀድሞ ያውቃቸዋል ፣ እንዳዲስ መዝገብ ደርሶኛል ማለቱና መዝገቦቹን ልመርምር ማለቱ ተገቢ አይደለም” ሲሉ ተቃውመዋ፡፡ ዛሬ ማለዳ የተሰየመው ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ካደመጠ በኋላ በጉዳዩ ላይ ብይን ለመስጠት ለዛሬ ከሰዓት ቀጠሮ ሰጥቶ ነበር፡፡ ይህን አስመልክቶ ከሰዓት በኋላ ያናገርናቸው የተከሳሾቹ ጠበቃ ሄኖክ አክሊሉ ፍርድ ቤቱ ለአቃቤ ህግ የ15 ቀን የክስ መመስረቻ ጊዜ መስጠቱን አረጋግጠውልናል፡፡ በሌላ በኩል ፖሊስ በዛሬው ችሎት ”የ14 ቀን የምርመራ ጊዜ እፈልጋለሁ” በሚል በእነዚሁ በአራት መዝገቦች በተከሰሱ ተጠርጣሪዎች ላይ የምርመራ ጊዜ ጠይቋል፡፡ ተከሳሾቹም በእነ መስከረም አበራ መዝገብ የተከሰሱትን ዮርዳኖስ አለሜንና ታደለ መንግስቱን ጨምሮ በተለያየ መዝገብ የተከሰሱ በርካታ ተጠርጣሪዎች ናቸው፡፡ ፖሊስ “ብዙ ስራዎችን ብሰራም የሚቀሩኝ ነገሮች አሉ ፣ በተጨማሪም ወደ አማራ ክልል ያቀናው የምርመራ ቡድን ስራውን አላጠናቀቀም” ብሏል፡፡ “በተጨማሪም የሚቀሩን የቴክኒክና የፎረንሲክ ማስረጃዎችን ማሰባሰብ ስላለብን ተጨማሪ የ14 ቀን የምርመራ ጊዜ ይፈቀድልኝ” ሲል ጠይቋል፡፡ የተከሳሽ ጠበቆችም በምርመራ ቡድኑ የሚሰሩ ስራዎች አብዛኛዎቹ የተተናቀቁ በመሆናቸው ፖሊስ ተጠርጣሪዎችን አስሮ ማቆየት የለበትም ሲሉ ተከራክረዋል፡፡ ክርክሩን ያደመጠው ችሎቱም ለፖሊስ 10 የምመራ ቀናትን ፈቅዷል፡፡ በተመሳሳይ አቃቤ ህግ ከእነዚህ መዝገቦች ውስጥ በወንጀል አልፈልጋቸውም በማለቱ በእነ መስከረም አበራ መዝገብ የተከሰሱት የእናት ፓርቲ የፖለቲካ ዘርፍ ሃላፊ ዶ/ር አሰፋ አዳነን ጨምሮ የተወሰኑ ተከሳሾች በገንዘብ ዋስ እንዲወጡ ከሰዓት በኋላ ፍርድ ቤቱ መወሰኑን ጠበቃ ሰለሞን ገዛኸኝ ለሮሃ ቲቪ ተናግረዋል፡፡ በአማራ ክልል ልዩ ሃይልን ለማፍረስ ከተደረገው እንቅስቃሴና ፋኖን ትጥቅ ለማስፈታት ከተጀመረው ወታደራዊ ዘመቻ ጋር ተያይዞ በአማራ ጉዳይ ላይ ንቁ ተሳትፎ ያደርጋሉ የተባሉ ጋዜጠኞች ፣ ፖለቲከኞች ፣ የማህበረሰብ አንቂዎች፣ ፋኖዎችና ወጣቶች በአማራ ክልልና በአዲስ አበባ በብዛት መታሰራቸው ይታወቃል፡፡ ዘገባው የሮሃ ቲቪ ነው ። “ውድ የአሻራ ሚዲያ ቤተሰቦች የአሻራ ሚዲያ ቻናልን ላይክና ሰብስክራይብ በማድረግ ድጋፋችሁን ታሳዩን ዘንድ በአክብሮት እንጠይቃለን።” ለፈጣንና አዳዲስ መረጃዎች አሻራ ሚዲያ የአይበገሬዎቹ ልሳን:- // Youtube:- https://www.youtube.com/channel/UCPmgFzP2ZPmdGjHxXjigJaw // Facebook:- https://www.facebook.com/asharamedia24 // ቴሌግራም:- https://t.me/asharamedia24
Source: Link to the Post