የአማራ ህዝብ፣ ጎጃም ቀጠና በተለይም የጎንቻ፣ እነብሴ እና መካነ ሰላም ወጣቶች በካድሪዎች ትዕዛዝ የመከላከያ ሰራዊት ለአፈና እንዲገባ እየተሰራ መሆኑን አውቀው ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀረበ። የአማራ ሚዲያ ማዕከል (አሚማ) ግንቦት 3/2015 ዓ/ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ የአማራ ህዝብ ጎጃም ቀጠና በተለይም የጎንቻ፣ እነብሴ እና መካነ ሰላም ወጣቶች በካድሪዎች ትዕዛዝ የመከላከያ ሰራዊት ለአፈና እንዲገባ እየተሰራ መሆኑን አውቀው ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጥሪ ያቀረበው በቀድሞ ልዩ ኃይል አባላት የተቋቋመ መሆኑን የገለጸው የዓባይ ሸለቆ ዘብ ነው። የልዩ ኃይሉን መበተን ተከትሎ በቆራጥ የአካባቢው ተወላጅ ልዩ ኃይል አባላት የዓባይ ሸለቆ ዘብ በሚል የተደራጀው ኃይል ከአንጎት እስከ እነ እነገሽ፣ ከጎሸራ እስከ ወረያ ባለው ቀጠና ያለውን ህዝብ በማንቃት እና በማደራጀት ላይ መቆየቱ ተገልጧል። ይሁን እንጅ በወረዳ ፖሊስ እና ጉጅሊ ተደጋጋሚ ትንኮሳ እንደተደረገበት አስታውቋል። ለአራት ግዜያት በእነገሽ፣ በበር ላይ፣ አባ ሚኒወስ እና ወረያ አካባቢ የተደረገበትን የጉጅሊ እና ፖሊስ ከበባ ሰብሮ ካድሪ የላካቸውን ጉጅሌወች እስከመማረክ መድረሱን ጠቅሷል። የአደረጃጀቱን ዓላማ በበጎ አሳቢ ወንድሞቻችን በኩል ለወረዳ ካድሬወች ለማስረዳት በተደረገው ጥረት እና ተኩስ የከፈተው የመንግስት ኃይል ላይ ባሳየነው አቅም ምክንያት የወረዳ አመራሮች ጉዳዩን ለማቀዝቀዝ ፍላጎት እንዳላቸው ጠቁመዋል። ይሁን እንጅ ከምስራቅ ጎጃም አብርሃም አያሌው፣ ኮማንደር አያልነህ ተስፋዬ እና ጌትነት አለልኝ የተባሉ ካድሪዎች አባይ ድልድይ አካባቢ አድማ በታኝ በመላክ ሲያዋጉን አድረዋል ብሏል በማህበራዊ ሚዲያ ባጋራው መልዕክቱ። ለአማራ ህዝብ ነፃነት የተቋቋመው የዓባይ ሸለቆ ዘብ ሮብ ለሃሙስ አጥቢያ ግንቦት 2/2015 ሌሊት ተኩስ ከፍቶበት ባደረው ኃይል ላይ ተገቢ ምላሽ መስጠቱንም ጠቅሶ ይህን ተከትሎ ካድሪዎቹ መካናይዝድ የመከላከያ ጦር እንዲገባ ለመከላከያ አመራሮች ጥሪ እያደረጉ ይገኛሉ ሲል ገልጧል። የሬሽን አቅርቦት ችግር ያለበት መሆኑን በመግለጽ የአካባቢው ማህበረሰብ እንዲተባበረውም ጥሪ አድርጓል። የአማራ፣ በተለይም የጎጃም እና የአካባቢው ወጣቶች ሰላማዊ የትግል መንገዶችን በመጠቀም የትግሉ አካል እንዲሆኑ አስቸኳይ ጥሪ ቀርቦላቸዋል። “መጭው ታሪክ በእኛ እጅ ይፃፋል” እንዲል ዘመነ ካሴ ታሪካችንን እንፃፍ! እንተባበር! እንበርታ!” ብሏል።
Source: Link to the Post