
የደቡብ ምዕራብ ክልል መንግሥት ሠራተኞች ደሞዛቸው ያለ ፈቃዳቸው በመቆረጡ ምክንያት የሥራ ማቆም አድማ ጀምሩ። አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ መጋቢት 14 ቀን 2015 ዓ/ም አዲስ አበባ ሸዋ የደቡብ ምዕራብ ክልል ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በተለይ የመምህራንን ደሞዝ በማዘግየት ይቀርብበት የነበረው ተደጋጋሚ ቅሬታ፣ አሁን ላይ ከሠራተኛ ፈቃድ ውጭ ደሞዝ ወደ መቁረጥ መሸጋገሩ የመንግሥት ሠራተኞችን አስቆጥቷል፡፡ ሠራተኞቹ ፈቃደኛ ሳይሆኑ ለአንድ ዓመት ያክል በየወሩ ከደሞዛቸው ላይ 10 በመቶ እንዲቆረጥ የተላለፈው ውሳኔ ተግበራዊ ተደርጓል፡፡ ይህንንም ተከትሎ በከፋ ዞን አንዳንድ ወረዳዎች የሥራ ማቆም አድማ መደረጉ ተሰምቷል። ለልማት በሚል ምክንያት የመንግሥት ሠራተኛው ሳይስማማ የተጀመረው የደሞዝ መቁረጥ ቅሬታ የፈጠረው፣ ከሕግ አግባብ ውጪ የሆነና ከወቅቱ የኑሮ ውድነት ጋር የማይስማማ ሀሳብ በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡ መጋቢት 13/2015 የሥራ ማቆም አድማ አድርገው ሰልፍ ከወጡ የመንግሥት ሠራተኞች መካከል በከፋ ዞን የጊምቦ ወረዳ የሃይስኩል መምህራን ይገኙበታል፡፡ መምህራኑ እንደገለጹት፣ ክልሉ ከተመሠረተ ጀምሮ እስካሁን የዘለቀው የደሞዝ መጓተት ችግር ሳይፈታ፣ በችግር ላይ ችግር የሚፈጥር የደሞዝ መቁረጥ ውሳኔ መምህራንን በእጅጉ አስቆጥቷል፡፡ “ልማት የሚጠላ ሰው የለም” ያሉት መምህራኑ፣ መጀመሪያ የመንግሥት ሠራተኛው ራሱንና ቤተሰቡን በአግባቡ ማስተዳደር ሳይችል ደሞዝ መቁረጥ “ሳትሠሩ ሥሩ እንደማለት ነው” ሲሉ አቋማቸው አስታውቀዋል፡፡ ገንዘብ የማዋጣት ሐሳቡ ከክልሉ መንግሥት እንደቀረበ፣ ከመንግሥት ሠራተኛው ጋር በተደረገው ውይይት መሠረት መንግሥት ሠራተኛው በፍቃደኝነት ላይ ተመሥርቶ፣ አቅሙ የፈቀደውን ገንዘብ የማዋጣት ሐሳብ አቅርቦ ነው የሚል ሐሳብ ተሰምቷል፡፡ ይሁን እንጂ በአንጻሩ መንግሥት ሠራተኛው ሳይስማማ ነው ደሞዝ የተቆረጠው በማለት በመቃወም ሥራ የማቆም እድማ እንቅስቃሴው ተጀምሯል ተብሏል፡፡ ይህን ተከትሎም ሠራተኞች ለክልሉ ዕምባ ጠባቂ ተቋም ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ የሠራተኛ ደሞዝ የሚቆረጥበት ሁኔታን በተመለከተ በሕግ የተደነገገው፣ ሠራተኛው እንዲቆረጥ የፈቀደውን መጠን ካስቀመጠና ይሁንታውን በፊርማ ካረጋገጠ ብቻ ነው፡፡ አዲስ ማለዳ እንደዘገበው።
Source: Link to the Post